የትምህርቱ ርዕስ | ከሐፍረት መዳኛችን

“ጌታ ሆይ ፥ በአንተ ላይ ኃጢአት ስለ ሠራን ለእኛና ለነገሥታቶቻችን ለአለቆቻችንና ለአባቶቻችንም የፊት እፍረት ነው ።” ዳን. 9 ፡ 8 ።

ጌታ ሆይ ! ያሉትን ደጎች እየገደልን የሞቱትን ደጎች እናከብራለን ። ታማኝነትን ጥለን ታማኞችን እንናፍቃለን ። ዕድላችንን ለዓለማዊነት ሰጥተን ልጆቻችንን ለመንግሥተ ሰማያት እናጫለን ። የተረፈንን ለመስጠት ተቸግረን ዋናቸውን ለምን አልሰጡም ? ብለን በሌሎች ሀብት እናዝዛለን ። የራሳችንን ድሆች ባዕድ እንዲረዳልን እንከጅላለን ። የደስታ እንጂ የመከራ ወዳጅ መሆን አቅቶን የታሰሩትን ወዳጆቻችንን እንሸሻለን ። እንዳይኖሩ የፈረድንባቸውን እንዲያስቡ እንመኛለን ። የራሳችንን ፈተና ወድቀን ለሰዎች መፈተኛ ገደል እናዘጋጃለን ። ያየናቸው ሕፃናት ላይ ጨክነን አዲስ ልጆችን ወደ ዓለም ለማምጣት እንሻለን ። እንዲሁ መካድ ስንችል የፖለቲካውን እሳት ለማግኘት ምለን እንክድሃለን ። ለመመስከርም ምለን ፣ ለመካድም ምለን እንዴት እንችለው ይሆን ?

ከኃጢአት በመመለስ ፣ ጽድቅን በመከጀል እኛም ተምረን ፣ አንተም መሐሪ ትባላለህ ፤ አሁን ግን ወንድ መባል በልጦብን ፣ ዲያብሎስን ለመምሰል መጸጸትን ጠልተናል ። ጽድቁ ያለው አንተ ጋ ሳለ በሰው ላይ በመፍረድ ተጠምደናል ። “እገሌማ ካልተቀጣ እኔ አልጠየቅም” ብለን በክፉዎች ትከሻ ተከልለን ለመትረፍ እንሞክራለን ። እውነትን በመላምቶች ተክተናል ። አየር አስገብተን እስክናስወጣ በመርዶ ዜና ተይዘናል ። እባክህ ጌታ ሆይ ፈጥረህ ላልፈጠሩን ጨካኞችና አዋቂዎች አሳልፈህ አትስጠን ።

ዓለም መራራ ብትሆንም በአገራችን ሰማይ ላይ የሚወጣው ፀሐይ እጅግ ያሳርራል ። የዘመን ፍጻሜ ላይ ብንሆንም የመከራችን ልክ ግን መስመር አጥቷል ። የሰው ደግነት ከሚታደገው በላይ አልቃሾቻችን በዝተዋል ። ታተርፈናለህ ብለን ወደ አንተ መጥተናል ። የዘመድ ገራፊ የሚያመውን ቦታ ስለሚያውቀው እጅግ ያሳምማል ። ከራስ እስከ እግር ያለው በሐፍረት ተመትቷል ። አንተን የሚያህል አምላክ ፣ እኛን የሚያህል ደካማ የለምና በዓይነ ምሕረት ተመልከተን ። ዓለም ሲጨልም ዓለማችን በሆንከው ፣ ሞተህ ዓለምን ባዳንከው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ለዘላለሙ አሜን !

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
መጋቢት 21 ቀን 2015 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም