መግቢያ » ልዩ ልዩ ሁለት » ስመ ብዙ ዮሐንስ መጥምቅ

የትምህርቱ ርዕስ | ስመ ብዙ ዮሐንስ መጥምቅ

ዮሐንስ ካህን ነው ። በብሉይ ኪዳን የክህነት ሐረግ ቢሄድ ሊቀ ካህናት የሚሆን የአባቱን መንበር የሚወርስ ነው ። እርሱ ግን ሊያድኑ የማይችሉ የብሉይ ኪዳን መሥዋዕትን የሚያሳርግ ሳይሆን የአዲሱን ኪዳን መሥዋዕት ክርስቶስን የሚያስተዋውቅ ሐዲስ ካህን ነው ። ክርስቶስ በግ ሁኖ ቢመጣ እርሱን የሚያሳርግ ካህን ግን አልነበረም ። ስለዚህ ራሱ ካህን ፣ ራሱ መሥዋዕት ፣ ራሱ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር መሥዋዕት ተቀባይ ሁኖ አዳነን ። እንዲህ ያለ ካህን አላየንም ። ምሕረት የሚሰጥ ፣ ለዘመኑ ፍጻሜ የሌለው ፣ ዐረፍተ ዘመን የማይገታው ካህን አላየንም ። ክህነትና ንግሥና በሕግ ተለያይተዋል ። ከሕግ በላይ የሆነው ፣ ሕግን የሰጠው እርሱ ግን ካህንም ንጉሥም ነው ። አንድ ጊዜ የተሠዋው ይህ በግ ወደ ኋላ ተመልሶ ከአዳም ጀምሮ ያሉትን ያዳነ ፣ ወደ ፊት ገሥግሦ እስከ ምጽአት ያሉትን ኃጢአተኞች የሚቀበል ነው ። ዮሐንስ ካህን ነው ። ካህኑ ዮሐንስ ሊቀ ካህኑን አስተዋወቀ ።

ዮሐንስ ባሕታዊ ነው ። ብቸኛ/ባሕታዊ ነው ሲባል ሰው ጠልቶ ገዳም የገባ አይደለም ፣ የጸሎት ዘብ ለመሆን የመነነ ነው ። ወታደር በበረሃ ተቀምጦ አገሩንና ሕዝቡን ይጠብቃል ። ወታደር የሚጠብቀው ከሚታይ ጠላት ነው ። ዮሐንስና የመንፈስ ልጆቹ ግን በብሕትውና ሆነው ሕዝባቸውን በጸሎት ይጠብቃሉ ። የጸሎት መሣሪያም ከሚታይና ከማይታይ ጠላት የሚታደግ ነው ። አገርን በጸሎት የሚጠብቁ ያስፈልጋሉ ። በጸሎት ማማው ላይ ሁነው ከሩቅ የሚመጣውን ጠላት ዓይተው የሚያስጠነቅቁ ጕበኞች/ጠባቆች/ ያሻሉ (ኢሳ. 20 ፡ 11 ።) ጸሎተኞች መኖራቸው ከራሳቸው ይልቅ ለእኛ አስፈላጊ ነው ። ሐዋርያው ሞትን መንገድ አድርጎት “ልሄድ እፈልጋለሁ” አለና፡- “ነገር ግን በሥጋ መኖሬ ስለ እናንተ እጅግ የሚያስፈልግ ነው” አለ ። (ፊልጵ. 1 ፡ 24 ።) የእግዚአብሔር ሰዎች ይበልጥ በዚህ ዘመን መኖራቸው ለእነርሱ ጉዳት ነው ። ለእኛ ግን አስፈላጊ ነው ። “እግዚአብሔር ሆይ ! ያንተን ሰዎች አታሳጣን” ብለን መጸለይ መልካም ነው ።

ዮሐንስ ሐዋርያ ነው ። ከሐዋርያት በፊት የነበረ ሐዋርያ ነው ። ሐዋርያ የክርስቶስ ምስክር ነው ። ዮሐንስም ስለ ክርስቶስ መሥክሯል ። ሐዋርያ ሂያጅ ፣ ገሥጋሽ ነው ። የምሥራቹን ይዞ ማደር የማይሆንለት ነው ። ተአምር ቢያደርግ ፣ በአዲስ ቋንቋ ቢናገር ግቡ ክርስቶስን በሰው ልብ ማንገሥ ነው ። ዮሐንስ ዝቅ ብሎ ክርስቶስን ያሳየ ነው ። ሰባኪው ረጅም ነው አሉ ። ከሰባኪው ጀርባ የክርስቶስ ሥዕል አለ ። እናቱ ይዛው ወደ ቤተ ክርስቲያን የምትሄደው ሕፃን ልጅ፡- “እማማ ይህን ሰባኪ አልወደውም” አላት ። እርስዋም ደንግጣ “ለምን ?” አለችው ። “ቁመቱ ረጅም ስለሆነ ክርስቶስን ይከልለኛል” አላት ። ዛሬም ቁመታቸው ረጅም ሆኖ ክርስቶስን የከለሉ ይኖራሉ ። ምሕረት የለሽ ሆነው እንደ መጋዝ ሲሄዱም ሲመለሱም የሚቆርጡ/ የሚበሉ ፣ የሚነግዱ አይታጡም ። ዮሐንስ ሐዋርያ ያውም ክርስቶስን ያሳየ ነው ። የጌታችን ሐዋርያት አብዛኞቹ የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ነበሩ ። ጴጥሮስ ፣ እንድርያስ ፣ ዮሐንስ ፣ ያዕቆብ ፣ ፊልጶስ ናትናኤል እነዚህ ሁሉ የዮሐንስ መጥምቅ ደቀ መዛሙርት ነበሩ ።

ዮሐንስ ካህን ነው ። በሰው ድካም የማይሳለቅ ፣ የሰውን ገመና አደባባይ የማያሰጣ ፣ በሰው ቍስል የማይነግድ ካህን ነበረ ። ግን የካህን ምልክት የሚሆኑ ወርቀ ዘቦ ልብሶች አይታዩበትም ። “ወንበሩ ንጉሥ አያደርግም” ይባላል ። ሰው ዙፋን አሠርቶ በቤቱ ሊቀመጥ ይችላል ። ወንበሩ ግን ንጉሥ አያደርገውም ። ካህንን ካህን የሚያሰኘው የክህነት ወጉ ነው ። “አዋላጅና አዋቂ ያየውን ሁሉ አይናገርም” ይባላል ። የእግዚአብሔር ካህን የክርስቶስ እንደራሴ ነውና የሰውን አበሳ ይሸፍናል ። ሰውዬው ቢጋለጥ እንኳ መሥዋዕት ሆኖ ያስጥለዋል ። ሐኪም በር ዘግቶ ያክማል ፣ የሥነ ልቡና አማካሪም ምሥጢር ጠብቆ ይረዳል ። ዛሬ ግን ቪድዮ እየቀረጹ የሚያናዝዙትን ፣ አገልጋይ ነን የሚሉትን ስናይ ፤ የቤተ ክርስቲያን የበላይ ጠባቂዎች መንጋውን እንደ ተዉት ፣ ክርስቶስን እንደገና በአደባባይ ዕርቃኑን እየሰቀሉት እንደሆነ ምስክር ነው ። ዮሐንስ መጥምቅ በአደባባይ ነገር ግን ወደ ትከሻው እያቀረበ ኑዛዜ ይሰማ ነበር ። በወራጁ መሐል ያሉት ዮሐንስና ያ ምስኪን ኃጢአተኛ የሚነጋገሩት እንዳይሰማ የወንዙ ድምፅ ይከለክል ነበር ።

ዮሐንስ መጥምቀ መለኮት ይባላል ። ከሁሉ የሚልቀው የማዕረግ ስሙ ይህ ነው ። ደግሞም መንገድ ጠራጊ ይባላል ። ስሙን በሹመት ያገኘው ሳይሆን በተግባር ያገኘው ነው ። ሰውን የሚገልጠው ሹመቱ ሳይሆን ጠባዩ ነው ። ጥምቀት ይህን ሁሉ ምሥጢር ይዟል ።

አቤቱ ሕዝብህን አድን !

ይቀጥላል

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ጥር 29 ቀን 2016 ዓ. ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም