መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሕይወት ሥነ ሥርዓት » የሕይወት ሥነ ሥርዓት (28)

የትምህርቱ ርዕስ | የሕይወት ሥነ ሥርዓት (28)

14. ቀጠሮ አክብር

ቀጠሮ የተጀመረው በእግዚአብሔር ነው ። ይህ ዓለም በመለኮታዊ ቀጠሮ የተፈጠረ ዓለም ነው ። ዘመን የሌለው ጌታ ዘመንን ለሰዎች ሰጠ ። ሰው በበደል በወደቀ ጊዜ ለመዳን ቀጠሮ ተሰጠው ። ሰው ከእግዚአብሔር ሳይለይ ከእግዚአብሔር ተለየ ። ለሆዱ እንጀራን ፣ ለአፍንጫው እስትንፋስን የሚያገኘው ከእግዚአብሔር ነው ። እንኳን በምድር በሲኦልም የሚኖረው በእግዚአብሔር ሕይወት ነው ። ጌታችን ወደ ምድር የመጣው ለሰዎች እንጀራ ለመስጠት ሳይሆን ራሱ ኅብስተ ሕይወት መሆኑን ለመግለጥ ነው ። 5500 ዘመን ሰው እንጀራ እየበላ ነበር ። ነፍሱ ግን ስደተኛና ረሀብተኛ ነበረች ። ሰው እግዚአብሔርን የሚክደው ከእግዚአብሔር የተቀበለውን እስትንፋስ መልሶ ሳይሆን በእግዚአብሔር ሕይወት ላይ ቆሞ ነው ። “በማን ላይ ቆመሽ ማንን ታሚያለሽ!” ይባላል ። እርሱ የካዱትን ቢክድ ኖሮ ፍጥረት በምድር ላይ ባልቆየ ነበር ። እግዚአብሔር ቀጠሮን መጀመሩ ብቻ ሳይሆን የሺህ ዘመናት ቀጠሮን የሚሰጥ አምላክ ነው ። የሰው ልጅ በምድር ላይ ከሚኖረው ዕድሜ የረዘመ ቀጠሮ ተሰጠው ። ይህ ብዙ ፍቺ አለው ። የመጀመሪያው የሰው የህልውናው መጨረሻ መቃብር አይደለም ። በሥጋው ያጣውን በነፍሱ ሊክሰው የሚችል አምላክ አለው ። ዛሬ በሥጋ ጉድለታችን ስንፈራ ስንጨነቅ ጌታ ግን አይጨነቅም ። ምክንያቱም በሰማይም ሊጋብዘን ይችላልና።

እኛ ምንም ሳናደርግላቸው የሄዱት ወገኖቻችን የእግር እሳት ሆነውብን ይሆናል ። ደግነታችንን መቃብር ገድቦት ይሆናል ። በሰማያዊው ዓለምም የሚሰጥ አምላክ ግን ሞት ገደቡ አይደለም ። ከሰው ዕድሜ የሚረዝመው ቀጠሮ ለምን ተሰጠ ካልን ከ5500 ዘመን በኋላም የሚኖረው ሰው አዳም ስለሆነ ነው ። ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ከእናንተ ጋር ነኝ ያላቸው እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚኖሩ ሆነው አይደለም ። የእነርሱን ሥራ የሚያስቀጥል ሁሉ ሐዋርያ ስለሆነ በደቀ መዛሙርቶቻችሁ ላይ አድሬ እሠራለሁ ማለቱ ነው ። ስለዚህ ጴጥሮስ ይህን ሲሰማ ብሞትም ሕያው ነኝ ፤ የመንፈስ ልጅ አለኝ ብሎ ይጽናናል ። የአዳምን ቀጠሮ ክርስቶስ ሲሰቀል የነበሩ ሁሉ ፍጻሜውን አይተዋል ። አንድ አዳም ነን ። አንድ ስለሆንን የአዳም በደሉና ጥፋቱ አግኝቶናል ። የአዳም መዳኑና ካሣው ነጻ አውጥቶናል ። በሞት አንድ ሁነን በኑሮ መለያየታችንና መከፋፋታችን ይገርማል ።

የእግዚአብሔርን ቀጠሮ ልዩ የሚያደርገው የማይረሳ አምላክ መሆኑ ነው ። እኛ ቀጠሮአችንን በመርሳት ፣ ባለመመቸት ፣ ባለመፈለግ ፣ በመስጋት ፣ ሌላውን ጉዳይ በማስበለጥ እንሰርዛለን ። እግዚአብሔር ግን መርሳት የሌለበት የሕሊናት ሁሉ ባለቤት ነው ። አይመቸውም አይባልም ፣ እርሱ የሌለውን ና ብሎ መጥራት የሚችል አምላክ ነው ። በሰጠው ተስፋ አይጸጸትምና አልፈልጋችሁም አይለንም ። የሚሽረው የለምና አይሰጋም ። የዘላለም ጉዳዩ እኛ ነንና የእርሱ ውዶች ነን ። እግዚአብሔር ቀጠሮን የሚያከብር አምላክ ነው ። የእርሱ ተከታዮች እርሱን ይመስላሉና ቀጠሮን ያከብራሉ ። “ነገር ግን የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ከሕግም በታች የተወለደውን ልጁን ላከ፤” ገላ 4፡4 ።

አንተም ቀጠሮ መስጠትን ልመድ ። ምክንያቱም አንተ እንደ ተመቸህ ያ ሰው አይመቸውምና በድንገት ውረድ ፍረድ አትበል ። ዓመት ሙሉ የረሳኸውን ሰው ዛሬ ስታገኘው አልላቀቅህም ብለህ ስሜታዊ አትሁን ። ቀጠሮ መስጠት ለሰውዬው ምቾት ፣ ለጉዳዩ ክብደት ነው ። ቀጠሮ በሰጠህ ጊዜ ወዳጅህ ተኝቶ እንዲያድር ወይም ተዘጋጅቶ እንዲመጣ ርእሱን ንገረው ። የምፈልግህ በዚህ ምክንያት ነው ብለህ አሳውቀው ። ምናልባት ስጦታ ልትሰጠው ሊሆን ይችላል ። ለምን እንደ ቀጠርከው ካላወቀ ግን የሞት ያህል ያስጨንቀዋል ። ስትቀጥረውም አንተም እርሱም የማትረበሹበት ቦታ ይሁን ። ያ ወዳጅህ የማይፈልገው ሰው ካለ ይዘህበት አትሂድ ። የማይፈልገውና ከዚህ በፊት ተነጋግራችሁበት የተዘጋ ነገርን አታንሣበት ። የቀጠሮውን ርእስ ለመንገር የማይቻል ከሆነ በሻይ ቡና ርእስ አግኘው ። እየጋበዝህ ግን ነገር አታብላው ። በምድር ላይ እጅግ ባለጌ የሆኑ ሰዎች ምግብ እየጋበዙ ነገር አብረው የሚያበሉ ናቸው ። አንድ ኪሎ ሥጋ ጋብዘው አራት ኪሎ ሚጥሚጣ ነስንሰው ይሄዳሉ ።

ቀጠሮ ስትሰጥ ያ ሰው ተጨንቆ እንደሆነ ለማረጋገጥ “ይመችሃል ወይ?” ብለህ ጠይቅ ። ምቾቱን ፍላጎቱን የምትነካበት ሰው እየጠላህ ይመጣል ። ሰው ከምንም በላይ ነጻነቱን የሚወድድ ፍጡር ነው ። ቀጠሮ እጅግ አድርገህ አክብር ። ቀጠሮህን እንዳትረሳ የሚያስታውሱ ማስታወሻዎች አድርግ ። በጸሎት ስፍራህ ወይም በቢሮህ ጠረጴዛ ላይ የቀጠሮህን ወረቀት አስቀምጥ ። ሊያነቃህ የሚችል ደወል ሙላ ። ሴቶች በማስታወስ ጎበዝ ናቸውና አስታውሱኝ ብለህ ንገራቸው ። ቀጠሮ ማክበር የመንፈሳዊነትም የሥልጣኔም መለኪያ ነው ። ምናልባት ያ ሰው ቢያረፍድ ደግሞም ቢቀር ጊዜህን እንዳታባክን የምትሠራውን ሥራ ፣ የምታነበውን መጽሐፍ ይዘህ ውጣ ። ቀረ ብለህ አትቀየም ። ለሰውም አትናገር ። ምናልባት በአደጋ ተሰናክሎ ይሆናል ። ወደ ቀጠሮህ ስትሄድ ጸልይ ። ንግግር ከመጀመራችሁ በፊትም ከዳኅፀ ልሳንና ልቡና እንዲሰውርህ አምላክህን ለምን ። በይበልጥ ለመጨዋወት ቀጠሮ መያዝ መልካም ነው ። አንዳንድ ጉዳዮች በስልክም ሊያልቁ ይችላሉና ለሁሉም ነገር ቀጠሮ ይያዝልኝ አትበል ። ዶሮ በጋን እንዳይሆንብህ ።

ሰው እፈልግሃለሁ ሲልህም አትኩሮት ስጥ ። ምናልባት ላለመኖር እየወሰነ ይሆናል ። ያንተ ቀጠሮ የሰውን ዕድሜ ማስቀጠል ከቻለ ከዚህ በላይ የምትኖርበት ዓላማ የለም ። ዛሬ ቢሞት ለመቅበር ይመችሃል ፣ ተጨንቄአለሁ ሲልህ አይመቸኝም አትበለው ። ያለችው ቀን ይህች ብቻ ልትሆን ትችላለች ። ብቻ ቀጠሮ አክብር ። ክቡርነትህን ማሳያ ነው ። ወላጆችህ ቀጠሮ ይከብዳቸው ነበር ። ሌሊቱን ሙሉ ሳይተኙ ሲንቆራጠጡ ያድሩ ነበር ። የሰውን ዋጋ ስላወቁ ዕድሜ ተሰጣቸው ። ለሰው ክብር የሌለው ዘመኑ አጭር ነው ።

ይቀጥላል
ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
ግንቦት 26 ቀን 2016 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም