ኤዶም የዔሳው ስም ነው ። ኤዶምያስ የዔሳው ዘሮች የሚጠሩበት ስም ሲሆን እነርሱ የኖሩበት ሴይርም ኤዶምያስ ተብሎ ይጠራል ። ኤዶም ማለት ቀይ ማለት ነው ። በቀይ ወጥ ብኵርናውን ስለሸጠ ዔሳው ኤዶም ተብሏል ። ዘፍ. 25፡30 ። ዘሮቹም እስራኤል ከግብጽ በወጡ ጊዜ አላሳልፍ ያሉ ፣ በተለያየ ዘመን የእስራኤልን መንግሥት የተፈታተኑ ነበሩ ። በመቃብያን ዘመን ተገርዘው ወደ እስራኤል የገቡ ሲሆን ሄሮድሳውያንም የኤዶም ዘሮች ነበሩ ። ሄሮድሳውያን ታላቁን ቤተ መቅደስ በማደስ ፣ የቤተ ልሔምን ሕፃናት በማስፈጀት ፣ ጌታችን ሲሰቀል ሐሰተኛ ፍርድ በመስጠት ይታወቃሉ ። ከአንዱ አብርሃም የተወለዱ እስማኤልና ይስሐቅ አንዱ በጣዖት የሚያምን አንዱ በሕያው ጌታ የሚያምን ነበሩ ። ከቡሩኩ ይስሐቅ የተወለዱም ያዕቆብ የተወደደ ፣ ዔሳው ደግሞ ለመንፈሳዊ ነገር ክብር ስላልነበረው በእግዚአብሔር የተጠላ ነበር ። አንዱ ክብርን ሲመርጥ ፣ አንዱ ውርደትን ይመርጣል ። የእናት ሆድ ዝንጉርጉር እንዲሉ ከአንዱ ምንጭ ሁለት ዓይነት ጅረት ይፈስሳል ። መንፈሳዊነት ከቤተሰብ ብንወርሰውም በምርጫ የምንቀጥልበት ነው ። ቅድስና በዘር አይተላለፍም ፣ በምርጫ እግዚአብሔርን የምንመስልበትም ነው ። ጕበኛ ማለትም ጠባቂ ማለት ነው ። ሴይር ማለት ጠጉራም ማለት ነው ፣ ዔሳው ጠጉራም ነበርና እርሱን የሚገልጥ ነው ። አሁንም ሴይር ማለት ዐውሎ ነፋስ ማለት ነው ። ስፍራው ዐውሎ ነፋስ ስለማይለየው የተሰጠው ስያሜ ነው ይላሉ ።
የእግዚአብሔር ሰዎች ከእግዚአብሔር የተቀበሉትን መልእክት ሸክም ይሉታል ። ሸክም አደራ ነው ፣ የእግዚአብሔር ቃልም የአደራው ቃል ነው ። ሸክም ከዚህ ወደዚያ የሚደርስ ነው ፣ የእግዚአብሔር ቃልም ከእግዚአብሔር ወደ ሰው የሚደርስ ነው ። ሸክም የማያሳርፍ ነው ፣ ቃሉም እስኪያደርሱት የሚያስጨንቅ ነው ። ሸክም ያለ ቦታው አይወርድም ፣ ቃሉም ወደ ተላክንበት ሕዝብ መድረስ አለበት ። ሸክም የሚያጎብጥ ነው ፣ ቃሉም ኃላፊነት ያለበት ነው ። ሸክም የማያስተኛ ነው ፣ ቃሉም አጥንትን የሚቆጠቁጥ ነው ። ኢሳይያስ ስለዚያ ሕዝብ ሸክም ነበረው ፣ ሸክም ተሰጥቶት ነበር ። እስራኤልን መንገድ አላሳልፍም ላለ ፣ የእስራኤልን ልዑላዊነት ለተዳፈረና የአምልኮ ነጻነቷን ለተጋፋ ሕዝብ ሸክም ይሰማው ነበር ። የእግዚአብሔር ፍቅር ፣ ቃሉና ጸሎት ድንበር የላቸውም ። በጸሎት ወገናዊ እንደመሆን እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ነገር የለም ። ቤተ ክርስቲያን ለእንስሳትና ለአፍላጋት ሳይቀር ትጸልያለች ።
ጠያቂው ከሴይር ነው ። ተጠያቂው ኢሳይያስ ሳይሆን አይቀርም ። ጠያቂው ደጋግሞ ይጠይቃል፡- “ጕበኛ ሆይ ፥ ሌሊቱ ምን ያህል ነው ? ጕበኛ ሆይ ፥ ሌሊቱ ምን ያህል ነው ? ብሎ ጠራኝ ።” የሌሊቱን ሰዓት የሚጠይቅ እንቅልፍ የከዳው ነው ። ሰዓት ስለሌለው እየጠየቀ ነው ። የሚጠየቀው ደግሞ ጕበኛው ነው ። ጕበኛው የከተማው ጠባቂ ነው ። ከፍ ባለ ማማ ላይ ተቀምጦ ፣ ሰላይ አሰማርቶ ፣ በአራቱም ማዕዘን ወደ ከተማይቱ ያለውን እንቅስቃሴ እያየ ለንጉሡና ለሕዝቡ የሚያመለክት ነው ። የሌሊቱን ሰዓት የሚጠይቀው ሰው ከቤቱ ወጥቶ የከተማው በር ላይ ሂዷል ። የሚጠይቀው ከሴይር ከኤዶም ወገን የሆነ ሰው ነው ። ጕበኛው ሕዝቡን በጸሎትና በትምህርት የሚጠብቅ ነው ። በጸሎት ከተዋጊዎች ፣ በትምህርት ከራስ አለማወቅ ወገንን የሚጠብቅ ነው ። ሕዝቡ ሲተኛ እርሱ ይነቃል ። ሕዝቡ ሰላም ነው ሲል ጉበኛው ከሩቅ እየመጣ ያለውን ያያልና ያለቅሳል ። ንጉሥና ሕዝብ አደራ የጣሉበት ወይም አደራ የተሰጡት ለማንቃትም የሚተጋ ነው ። አገርን አርግዞ ፣ ንጉሥን ሳይቀር የሚጠብቅ ነው ። እንደ ጋሪ ፈረስ ወደ አንድ አቅጣጫ ብቻ የሚያይ ሳይሆን እየተሽከረከረ በአራቱም ማዕዘን የሚመለከት ነው ። ጕበኛው ሌሊት ብቻውን ሲሆን ይጸልያል ፣ ቀን ሕዝቡን ያስተምራል ። በከተማው በር ላይ ኑሮውን መሥርቷልና የተጣሉትን ያስታርቃል ፣ የቄሣርን ለቄሣር ስጡ ይላል ። አምሽተው የመጡትን ይመልሳል ። ጠላት እንዳይገባ በሩን ይዘጋል ። የእግዚአብሔር ሰዎች ጕበኛ ወይም ጠባቂ ናቸው ። የሩቁን ያያሉ ያሳያሉ ። እየመጣ ያለውን ጥፋት ያሳውቃሉ ። የእግዚአብሔር ሰዎች የአገር ዓይን ናቸው ።
ጕበኛውም፡- ይነጋል ደግሞም ይመሻል ትጠይቁ ዘንድ ብትወድዱ ጠይቁ ተመልሳችሁም ኑ አለ ።”
የጕበኛው ምላሽ የሚደንቅ ነው ። ንጋቱ ወዲያው እንደሚመሽ የሚያመለክት ነበር ። ንጋቱ አሦራውያን እስራኤልን ከለቀቁ ወይም ስጋታቸው ካበቃ በኋላ ትንሽ ጊዜ ዕረፍት ይሆንና ባቢሎናውያን ሕዝቡን ማጋዛቸውን የሚያመለክት ነው ። አሦራውያን ሰማርያን የያዙት ከክርስቶስ ልደት በፊት 722 ዓመት ነው ። ባቢሎናውያን ደግሞ በ586 ዓመት ኢየሩሳሌምን አፈረሱ ። ትንሽ ብርሃን ይሆናል ቀጥሎ ጨለማ ይሆናል ። ነግቶ ወዲያው መምሸቱን ያ ጠባቂ ተናገረ ። ቀጣዩን ለማወቅም ጠያቂ ካለ ኑ በማለት ይመክራል ። የዘመን ካርታ በጸሎተኛው እጅ ላይ ተቀምጧል ።
እስራኤል የገጠማት ፈተና አንዱ አገዛዝ ሲያልፍ ሌላኛው ጨምሮ የሚመጣ ነበር ። ነጋ ሲባል ወዲያው የሚጨልም ነበር ። የተፈጥሮ ሥርዓቱ እስኪዛባ ድረስ ከጨለማ በኋላ ጨለማ ይመጣ ነበር ። ይህን ያስተዋለው ግን ያ ጕበኛ ነበር ። አገር ሰንሰለታማ በሆነ ችግር ፣ መቆሚያ በሌለው ጅረት ውስጥ ስታልፍ መከረኛው ሕዝብ ይደነዝዛል ፣ የእግዚአብሔር ሰዎች ግን ጉዳዩን ያውቁታል ።
በአገራችንም ሌሊቱ የረዘመበት ወገን ብዙ ነው ። የሚጠይቀው የእግዚአብሔር ሰው ግን ያጣ ይመስላል ። ከሌሊቱ በኋላ ብርሃንን መስማት ሲናፍቅ ሌላ ሌሊት ይመጣል ፣ ብልጭ ብሎ የሚጨልም ነገር ይታያል ። የተጀመረ ነገር አይለቅላችሁ ተብሎ የተረገምን እስኪመስል ብርሃናችንን ጠብቀን መቆም ቸግሮናል ። ወጣ ወጣ ያሉ ቶሎ ይቀጫሉ ። ራእይ የሰነቁ መቃብር ይወርዳሉ ። የሚበጅ ነገር ያረገዙ ጽንሱም እነርሱም ይሞታሉ ። እኛም አውቀነው የምንጨፍረው ሲጀመር ነው ። የጨፈርንባቸው ጅማሬዎች ፍጻሜ አጥተው መሠረት ብቻ ሁነው ይታያሉ ። መከራችን ያለቀ እየመሰለን ብልጭ ባሉልን ቀኖች ደስ ስንሰኝ በሌላ በአዲስ ገራፊ እንሸማቀቃለን ። ሌሊቱ ምን ያህል ነው ብለን ለመጠየቅም የእግዚአብሔር ሰዎችን ንቀናል ፣ አሊያም የእግዚአብሔር ሰዎችን መለየት አቅቶናል ።
የባቢሎንን ቅኝ ያመጣው ሳምራውያን የሆኑት ወገኖቻቸው በአሦራውያን እጅ መሰቃየታቸውን አይተው መማር ባለመቻላቸው ነው ። እኛም በዙሪያችን ያሉ አገሮች “ውድቀት ማለት ምን ማለት መሆኑን” ፣ አገር አልባ መሆን ማለት እንዴት ያለ ውርደት መሆኑን እየነገሩን ነው ። ብልጭ የሚሉ ብርሃኖች ሙሉ ቀን ወደሚሆን ብርሃን እንዲያድጉ ፣ ከሌሊት በኋላ ሌሊት እንዳይመጣ ፣ ቀን እንዲበሰር የሚያግዝ ስለ አገርና ስለ ወገን ብርቱ ጸሎት ማቅረብ ነው ።
አዎ ይነጋል ደግሞ ይመሻል ።
አቤቱ ለእኛ ያደረከውን መልካም ነገር አጽናው ።
ዲያቆን አሸናፊ መኮንን
ሐምሌ 29 ቀን 2012 ዓ.ም.