የትምህርቱ ርዕስ | ራስን መግዛት

 “እንግዲህ ኤጲስ ቆጶስ እንዲህ ሊሆን ይገባዋል፤ … ራሱን የሚገዛ” 1ጢሞ. 3 ፡ 2
ብዙ ሰዎች የመግዛት ምኞት አላቸው ። እገሌ የገዛውን አገር እኔ መግዛት አያቅተኝም ይላሉ ። ብዙ ፖለቲከኞች አገር የመምራት እቅድም ዝግጅትም አላቸው ። አንድ ሰው ብቻ ቢቀመጥበትም የንጉሥን ወንበር አያሌዎች ይመኙታል ። በምድር ላይ ከኖርንበት ሰባ ዓመት አገር የምንመራበት አራት ዓመት ከባድ ፈተናና ትግል ያለበት ነው ። የቀላው የሚጠቁርበት ፣ የጠቆረው የሚነጣበት ፣ እየባነነ የሚኖርበት ፣ የዛፍ ላይ እንቅልፍ ቢሆንም ብዙ ሰው መግዛትን ይመኛል ። ሁሉ ሰው አገር አይገዛም ። ሁሉ ሰው ግን ራሱን መግዛት ይችላል ። ሰው በተፈጥሮው ገዥ ሁኖ ስለ ተፈጠረ ራሱን ሊገዛ ሌሎችን ሊመራ ይገባዋል ። አምባገነን ከሆነም በሥጋው ላይ ፣ ቊጡ ከሆነም በምኞቱ ላይ ሊሆን ይገባዋል ። አገር የገዙ ሰዎች ራሳቸውን መግዛት አልቻሉም ነበር ። አገር እየገዙም ራስ ሊያምፅ ይችላልና ራስን መግዛት ትልቅ ሥልጣን ነው ። በሰው ላይ የበላይ ከመሆን በአንደበታችን ላይ የበላይ መሆን የተሻለ ነው ።

ብዙ ጠባቂ ያለው ንጉሥ ዳዊት፡- አቤቱ፥ ለአፌ ጠባቂ አኑር ፥ የከንፈሮቼንም መዝጊያ ጠብቅ” ብሏል መዝ. 140፡3 ። ሕዝቡ ይጠብቀናል የሚለው ንጉሥ እርሱ መጠበቅ ያቃተው የገዛ አንደበቱን ነበር ። ሕዝቡ ጠባቂ ያኖርልናል የሚለው ንጉሥ እርሱ የከንፈሮቹን መዝጊያ እንዲጠብቅለት እግዚአብሔርን ይማጸናል ። ምነው ባልተናገርናቸው ብለን የምንጸጸትባቸው ቃላት አሉ ። ምነው ዱዳ ባደረገኝ ያልንባቸው ያመለጡን ንግግሮች አሉ ። ከባዱ ዝሙትን ፣ ከባዱ ስርቆትን እንቢ ማለት አይደለም ። ከባዱ አንደበትን መግዛት ነው ። ሰው አንደበቱን መቆጣጠር ከቻለ ሌሎች ኃጢአቶች አይከብዱትም ። አንደበት በልባችን ያለውን ብቻ ሳይሆን የሌለውንም የምናወጣበት ነው ። አስበን መናገር ሲያቅተን ተናግረን ማሰብ እንጀምራለን ። አንደበት ፈተና ማስገቢያም ነው ። በተናገርነው እንጠመዳለን ። በፈረድነው እንያዛለን ። ኤጲስ ቆጶስ ራሱን የሚገዛ መሆን ይገባዋል ።
መኪና ጎማ ብቻ ሳይሆን ማብረጃ ፍሬን አለው ። ማብረጃ ባይኖረው መኪና አደጋ ብቻ ይሆን ነበር ። ፈረስ ልጓም ፣ መኪናም ፍሬን አለው ። ሰውም ራሱን የሚቆጣጠርበት ትዕግሥት ሊኖረው ይገባል ። ራስን መግዛት የሚለው ቃል የገበያ ቋንቋም ነው ። መግዛትና መሸጥ የሚባሉ ቃላት የገበያ ቋንቋ ናቸው ። ሰው ንብረቱን ሊሸጥ ፣ ከብቱን ሊለውጥ ይችላል ። ራሱን ግን መግዛት አለበት ። ራስ አይሸጥምና ። ራስ አይለወጥምና ። የተሸጠ ነገር የገዛው ሰው እንደ ፍላጎቱ ይጠቀምበታል ። ራስን አለመግዛት ማለት ክፉ ተናግረው ክፉ ለሚያናግሩን ሰዎች ራስን አሳልፎ መስጠት ነው ። ገዝተውናልና እንዳሻቸው ይጠቀሙብናል ። እየተሳደቡ ተሳዳቢ ፣ እየተተናኮሉ ተንኮለኛ ፣ እየወረወሩ ድንጋይ ወርዋሪ ያደርጉናል ። ራስን መግዛት ራስን አለመሸጥ ነው ። ለዝሙት የተሸነፉ ሰዎች ራሳቸውን ሸጠዋል ። ልብስና አካል እያዩ ፣ የዝሙት ቅብዐ መንግሥት የሆነውን ሽቱ እየተከተሉ የነጎዱ እነርሱ ራሳቸውን ሸጠዋል ። ራሳችንን የምንገዛበት ዋጋ ከፍ ያለ ነው ። ከወርቅም በላይ ነው ። እርሱም ቅድስና ይባላል ።
ራስን መግዛት በብዙ መንገድ ያስፈልጋል ። ራስን መግዛት ሲባል አንድ ነገርን ወይም ፈቃደ ሥጋን ብቻ የሚመለከት አይደለም ። ራስን መግዛት መናኔ ንብረት መሆንም ነው ። ቅዱሳን አባቶቻችን ዘውድ አስቀምጠው ሲመንኑ ፣ ያላቸውን ለድሆች ሰጥተው የክርስቶስ ሙሽራ መሆንን ሲመርጡ ራሳቸውን ስለ ገዙ ነው ። ራስን መግዛት መተው ብቻ ሳይሆን መስጠትም ነው ። ራስን መግዛት ስርቆትን እንቢ ማለት ብቻ ሳይሆን መስጠትንም መፈለግ ነው ። ያዩትን ዕቃ የእኔ የሚሉ ፣ እንደ መንፈቅ ልጅ ሁሉን ላፌ በማለት የሚያስቸግሩ ራሳቸውን መግዛት ያልቻሉ ናቸው ። ይልቁንም በድህነት ያደገ ወርቅ አይጠግብምና መጠንቀቅ ያስፈልጋል ። ወርቅ የማይጠግቡ ነገሥታት ገዳማትን ዘርፈዋል ። የእግዚአብሔርን አሥራት ሰርቀዋል ። መቅደስ አቃጥለዋል ። ብዙ ትዳሮች የሚፈርሱትም በምኞታቸው ራሳቸውን በማይገዙ ሰዎች ምክንያት ነው ። ያገኙትን ልብስ ፣ የማያደርጉትን ጫማ እያግበሰበሱ ይዘው የሚገቡ ኑሮአቸው ላይ እክል ይገጥማቸዋል ። ራስን አለመግዛት አለመርካትን ያመጣል ። በየገበያ የሚያዞር አመል ያለባቸው ሰዎች አሉ ። ይህ መታከም ያለበት በሽታም ነው ። ተበድረው ፣ በዱቤ ያገኙትን ሁሉ አግበስብሰው ይገባሉ ። በዕቃ ላይ ራስን መግዛት ካልቻልን መተኛ ቦታ እስክናጣ ቤታችን ገበያ ይመስላል ።
ኤጲስ ቆጶስ ራሱን መግዛት አለበት ። የመነኮሳት ፆራቸው ስስት ነው ይባላል ። ጌታችን ስስትን በምድረ በዳ ድል ነሣ ። የቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪዎች እናትና አባታቸው እግዚአብሔር ነውና የሚጦር ልጅ ፣ የሚረዳ ዘመድ የለኝም ብለው ሊስገበገቡ አይገባም ። ምክንያቱም የሚሰብኩት አምላካቸው እንኳን ለሚያገለግሉት ለጠላቶቹም የሚመግብ ነው ። ስስት ራስን አለመግዛት ነው ። ገቢ እንጂ ወጪ አለመውደድ ራስን አለመግዛት ነው ። በስስት ምክንያት በቀላሉ ታክመው ሊድኑ ሲችሉ ከፍተኛ በሽታ በራሳቸው ላይ የጠሩ አሉ ። ራስን አለመግዛት መሰብሰብ ብቻ ሳይሆን በስስት ራስን መርዳት አለመቻልም ነው ።
ኤጲስ ቆጶስ አንደበቱን የሚገዛ መሆን አለበት ። እንኳን ክፉ ቃሉ ደግ ቃሉም ይተረጎማልና ትዕግሥተኛ መሆን አለበት ። ከእርሳቸው ይህን አንጠብቅም የሚሉ ብዙ ታዛቢዎች ሲኖሩ ጥቂት ሸፋኞች ማግኘት ከባድ ነው ። ሰው አገልጋይ ቢሆንም ሰውነቱ አይቀርም ። አገልጋይ የሚበላ ፣ የሚጠጣ ፣ የሚያዝን የማይመስላቸው ሰዎች አሉ ። ይህ ትልቅ አለማወቅ ነው ። ስሜት ተሸክመን የሌላውን ስሜት መረዳት አለመቻል ትልቅ ኪሣራ ነው ። ክፉ ንግግርን መናገር አብረው ለመኖርም ለመለያየትም አይጠቅምም ። አብረው የሚቀጥሉ ከሆነም እንቅፋትና ተጨማሪ ቅያሜ ነው ። የሚለያዩም ከሆነ ያለቀ ጉዳይ ነውና ራስን ማራቆት ነው ። “የጨዋ ልጅ ሲፋታ የሚጋባ ይመስላል” እንዲሉ ።
ለቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ ቶሎ ባለመወሰን ራስን መግዛት አስፈላጊ ነው ።አንድ ውሳኔ ከመወሰን በፊት ቢያንስ የሦስት ቀን ዕድሜ መስጠት ተገቢ ነው ። በቤተ ክርስቲያን ያለው ውሳኔ በአብዛኛው ነፍስን የሚመለከት በመሆኑ ጥንቃቄ ይፈልጋል ። መሾም ማለት ለመወቀስ ፣ ለመከሰስ ራስን አሳልፎ መስጠት ነው ። ስለዚህ ወቀሰኝ ፣ ከሰሰኝ ብሎ እንጀራ መንሣት ተገቢ አይደለም ። ሰው የሚከስሰውም እየበላ ነውና እንጀራን መንሣት ለአንድ ኤጲስ ቆጶስ ተገቢ አይደለም ። ከእኔ ይቅር እያለ መጓዝ ይገባዋል ። የራስን ስምና ክብር ማስጠበቂያ ሳይሆን የክርስቶስን ስምና ክብር መጠበቂያ መንበር መሆኑን ማሰብ ያስፈልጋል ።
ኤጲስ ቆጶስ ሹመት በመስጠት ራስን መግዛት ይገባዋል ። ወንጌልን ያልተማረና መንፈሳዊነት የጎደለውን ሰው ሳመኝ ፣ አወደሰኝ ብሎ መሾም ለቤተ ክርስቲያን በሽታ መፍራት ነው ። የእልህ ሹመቶች ቀጣዩን ትውልድ የሚበቀሉ ናቸው ። ኤጲስ ቆጶስ ከመጠን ያለፈ ውዳሴ የሚያቀርቡለትን መጸየፍ ይገባዋል ። እንደ እግዚአብሔር ቅዱስ የሚሉን እንደ ሰይጣን ርኵስ ሊሉን ቅርብ ናቸውና ። ይልቁንም የጉቦ ሹመት መስጠት ራስን ማዋረድ ፣ ትውልድን ለነጋዴ አሳልፎ መስጠት ነውና መጠንቀቅ ይገባል ። የቅን አገልግሎታችን ከሰው ዘንድ ዋጋ ባያገኝ እግዚአብሔርን ካስደሰተ በቂ ነው ።ኃይለኝነት የሚያስከብር ቢሆንም ትሕትና ግን ክብሯ ከሰማይ ነው ። መንፈሳዊ መሪ ትሑት እንጂ አምባገነን መሆን የለበትም ።
ለሁላችንም ራስን መግዛት ይስጠን ።
1ጢሞቴዎስ 36
ጥር 11 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም