የትምህርቱ ርዕስ | አንድ እግዚአብሔር አለ

“አንድ እግዚአብሔር አለና ፥ በእግዚአብሔርና በሰውም መካከል ያለው መካከለኛው ደግሞ አንድ አለ ፥ እርሱም ሰው የሆነ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው” 1ጢሞ. 2፡5
ሐዋርያው ጳውሎስ በኤፌሶን ላለው ጳጳስ ለልጁ ለጢሞቴዎስ ይህን አንደኛ ጢሞቴዎስን የጻፈለት በአገልግሎቱ ውጤታማ እንዲሆን ፣ የልብ ስብራት ደርሶበትም ከመንገድ እንዳይቀር ለማበረታታት ነው ። አንደኛ ጢሞቴዎስ ስድስት ምዕራፎች ያሉት ሲሆን፡-
·        ምዕራፍ አንድ ሃይማኖትን ስለ መጠበቅ ፣
·        ምዕራፍ ሁለት አምልኮተ እግዚአብሔርን በትጋት ስለ መፈጸም ፣
·        ምዕራፍ ሦስት እውነተኛ አገልጋዮችን ስለ መሾም ፣
·        ምዕራፍ አራት ስለ አገልጋይ መንፈሳዊ ቁመና ፣
·        ምዕራፍ አምስት ቤተሰብን ስለምትመስል ቤተ ክርስቲያን ፣
·        ምዕራፍ ስድስት የስብከት ዋነኛ አርእስትን ይናገራል ።

ሐዋርያው ጳውሎስ ሰዎች ሁሉ እንዲድኑና እውነቱን ወደ ማወቅ እንዲደርሱ የእግዚአብሔር መልካም ፈቃድ መሆኑን ተናግሯል ። ሰዎች ሁሉ የሚድኑበት ምሥጢርና የሚያውቁት እውነት ምንድነው ? ብሎ የሚጠይቅ ጠያቂ ካለ ሐዋርያው፡- “አንድ እግዚአብሔር አለና ፥ በእግዚአብሔርና በሰውም መካከል ያለው መካከለኛው ደግሞ አንድ አለ ፥ እርሱም ሰው የሆነ ክርስቶስ ኢየሱስ ነው” ይላል 1ጢሞ. 2፡5 ። ሐዋርያው አንድ እግዚአብሔር አለና ሲል ምሥጢረ ሥላሴን ፣ አንድ መካከለኛ አለ ሲል ደግሞ ምሥጢረ ሥጋዌን እየገለጠ ነው ። በምሥጢረ ሥጋዌ ሥርም ምሥጢረ ጥምቀት ፣ ምሥጢረ ቊርባንና ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታን አሉ ። ስለዚህ የጥምቀትና የቊርባን መሠረት ምሥጢረ ሥጋዌ ነው ። በጥምቀትም በቊርባንም በዋናነት የክርስቶስን ሞትና ትንሣኤ እንመሰክራለንና ። የምሥጢረ ሥጋዌ መሠረትም ምሥጢረ ሥላሴ ነው ። ሥጋዌን ልዩ ያደረገው አምላክ ሰው መሆኑ ፣ ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል ወልድ ፣ በተለየ አካሉ ሥጋ መልበሱ ነው ።
ሐዋርያው በአጭሩ ለመዳንና እውነቱን ለማወቅ ምሥጢረ ሥላሴንና ምሥጢረ ሥጋዌን እየተናገረ ነው ። ቤተ ክርስቲያን አምስቱ የሃይማኖት ምሰሶዎች /አምስቱ አእማደ ምሥጢር/ የምትላቸው ከመጽሐፍ የተገኙ ናቸው ።
አንድ እግዚአብሔር አለና ። የብሉይ ኪዳን ትልቁ የእምነት መግለጫ “እግዚአብሔር አንድ ነው” የሚለው ነው ። እስራኤላውያን በብዙ አማልክት በሚያመልኩ መካከል አንዱን አምላክ ማምለካቸው ልዩ ያደርጋቸዋል ። የብዙ አማልክት ተከታዮች እምነትና ድፍረት የላቸውም ። አንዱ አምላክ የሚቤዥ አምላክ መሆኑን እስራኤላውያን ከግብጽ የባርነት ቤት ሲወጡ ተረድተዋል ። አንዱ አምላክ የሠራነው ሳይሆን የሠራን ፣ የምንሸከመው ሳይሆን የሚሸከመን ነው ። ለፍጥረት መገኘትን ፣ ሥርዓትንና ነዋሪነትን፣ ደግሞም ፍጻሜ የሚሰጥ ነው ። ሰማይና ምድርን የፈጠረው አንዱ አምላክ መሆኑ በፍጥረት ስምምነት ይታወቃል ። ሌሊትና ቀኑ ፣ ሰማይና ምድሩ ያለ ግጭትና ያለ ሁከት የሚኖሩት አንዱ አምላክ ስለ ሠራቸው ነው ። ሰዎች ደግሞ በሁከት የሚኖሩት ብዙ አማልክትን ስለሚከተሉ ነው ። አንዱ አምላክ በሦስት ገጻት የሚኖር ፣ በሦስት አስማትና በሦስት አካላት የተገለጠ ነው ። አንድ አካል አንድ ቢባል የሚደንቅ አይደለም ። ሦስቱ አካላት አንድ መሆናቸው ግን ይደንቃል ። በዓለም ላይ ብዙ ሦስትነቶች ቢኖሩም የሥላሴ ሦስትነት ግን የተለየ ነውና ቅድስት ሥላሴ ወይም የተለየች ሦስትነት ብለን እንጠራዋለን ።
የእግዚአብሔር አንድነት የምንለው እግዚአብሔር በፈቃድ ፣ በተግባር ፣ ሕይወትን በመስጠት ፣ በመፍረድ ፣ በማፍቀር ፣ በመስጠት ፣ በመንሣት ፣ በመግደል ፣ በማዳን ፣ ዓለማትን በማምጣት ፣ በማሳለፍ ፣ በባሕርይ ፣ በህልውና ፣ በመለኮት ፣ በአገዛዝ ፣ በረድኤት ፣ በተአምራት አንድ ነው ።
እግዚአብሔር በፈቃድ አንድ ነው ። እያንዳንዳቸው የሥላሴ አካላት የራሳቸው ልብ ፣ ቃል ፣ እስትንፋስ አላቸው ብለው የሚያስተምሩ የዘጠኝ መለኮት ትምህርት አራማጅ ናቸው ። እግዚአብሔር አንድ ልብ መሆኑ እግዚአብሔር በፈቃድ ፣ በመወሰን ፣ በምክር አንድ ነው ማለት ነው ። ፈቃዱ ከዘላለማዊነቱና ከቅዱስነቱ ይመነጫል ። ፈቃዱንም በመገለጥ ወይም በአስተርእዮ ለሰዎች ያሳውቃል ። አስተርእዮ ያስፈለገው እግዚአብሔር ራሱን ካልገለጠ ልናውቀው ስለማንችል ነው ። የአስተርእዮው መንገድ ነቢያት ፣ መጻሕፍት ፣ ተአምራት ፣ ቤዛነት ሊሆኑ ይችላሉ ። እግዚአብሔርም በራሱ ይታወቃል ፣ በአቅማችን ልክ ግን ለእኛ ተገልጧል ። እግዚአብሔርን ሙሉ በሙሉ ልወቀው ማለትና ጨርሶ ማወቅ አልፈልግም ማለት ሁለቱም ስህተት ናቸው ። እግዚአብሔር ታላላቅ ውሳኔዎችንም ወስኗል ። እነዚህም ሰውን መፍጠር ፣ ማዳንና ዳግመኛ መምጣቱ ናቸው ። ምክሩም የጸና ነው ። ከሕዝቦች ምክር ይልቅ የአንዱ እግዚአብሔር ምክር ይበረታል ። በምክራችን ላይ እርሱ ካልመከረበት ምክራችን ከንቱ ነው ። በምክሩ ግሩም የተባለም እርሱ ብቻ ነው ።
እግዚአብሔር የግብር አንድነት አለው ። በሥላሴ መንግሥት ግብር ሁለት ዓይነት ነው ። ውሳጣዊና አፍአዊ ይባላሉ ። ውሳጣዊ ግብር ሦስት ነው ። ይህም አብ ወላዲ ፣ ወልድ ተወላዲ ፣ መንፈስ ቅዱስ ሠራጺ የሚባልበት ነው። ይህ ውሳጣዊ ግብር ሦስት ነው ። አፍአዊ ግብር የሚባለው ግን ለፍጥረት የሚሰጠው ቸርነትና ማዳን ነው ። በዚህ ግብር እግዚአብሔር አንድ ነው ። በወልድ ቃልነት ዓለም ቢፈጠር ቃልነቱ ለአብም ለመንፈስ ቅዱስም ነውና ሥላሴን ፈጣሪ ያሰኛቸዋል ። በወልድ ቤዛነት ዓለም ቢድንም ሥጋ መልበስ የወልድ የተለየ ግብሩ ሲሆን ማዳን ግን የመለኮት አንድ ግብር ነውና ሥላሴ አዳኝ ይባላሉ ።
ብዙ ወጣቶች ኢየሱስ ብቻ የሚል ትምህርት ሲያስተምሩ ይታያሉ ። ሰባልዮስና የዘመናችን ኢንሊ ጂሰሶች ኢየሱስ ብቻ ይላሉ ። ይህ ስህተት ነው ። ስለ አንድ መካከለኛ ወይም አዳኝ ስንናገር ስለ አንድ አምላክ መርሳት የለብንም ። መዳናችን ሥላሴያዊ ነው ። በአብ ፍቅር ፣ በወልድ ቤዛነት ፣ በመንፈስ ቅዱስ ምስክርነት ድነናል ። ለዚህ ነው ታላቁ ባስልዮስ መዳን ሥላሴያዊ ነውና፡- “በአንድ ልጅህ በርሱ ያለ ክብርና ጽንዕ ላንተ ይገባሃል ፣ ከመንፈስ ቅዱስም ጋር ለዘላለሙ አሜን” የሚለውን ጸሎት የቀመረው ።
ሕይወት አንዲት ናት ። ሕይወትም የእግዚአብሔር ገንዘብ ናት ። ከሕያው ባሕርዩ የተነሣ ሕያዋንን ፈጥሯል ። ሥላሴ በመንፈስ ቅዱስ ሕይወትነት ይኖራሉ ። ይህ ሕይወትም ለሰውና ለመላእክት ተሰጥቷል ። ሕይወት ለእግዚአብሔር የባሕርይ ገንዘቡ ስትሆን ለሰው ግን ስጦታ ናት ። ሕይወትም በወርቅ እንዳትገዛ ከዋጋ በላይ ናት ። ከፍጡር እንዳንከጅላት ትርፍ ሕይወት ያለው ማንም የለም ። የሕይወት ምንጭ ግን እግዚአብሔር ነው ። ጣዖታት ግዑዛን ናቸው ። ሕያዋን ሰዎች ግዑዛንን ፈጠራችሁን ብለው ከሚያመልኩ ጣዖታት ሰውን ቢያመልኩ ይሻል ነበር ። እኛ ሕያዋን ነንና ሕያው አምላክ እንደፈጠረን ህልውናችን ምስክር ነው ። እግዚአብሔር በሕይወት አንድ ነው ። አንድ እግዚአብሔር አለ ። ብዙ እግዚአብሔር ቢኖር ኖሮ ዓለም ትታወክ ነበር ። ብርሃንና ኃይል በሚያመነጩ ተቋማት አካባቢ መኖር ይረብሻል ። ትልቋ ፕላኔትና ኃይል ሰጪ ፀሐይ ግን ድምፅዋ አይሰማም ። አንድ እግዚአብሔር ስላለ ፍጥረት በጸጥታ እየተጓዘ ነው ።
1ጢሞቴዎስ /25/
ታኅሣሥ 20 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም