የትምህርቱ ርዕስ | የኃጢአተኞች ወዳጅ

“ኃጢአተኞችን ሊያድን ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነና ሁሉ እንዲቀበሉት የተገባ ነው ፤ ከኃጢአተኞችም ዋና እኔ ነኝ፤” 1ጢሞ. 1፡15
ትዕቢት ከእግዚአብሔር መራቅ ነውና ሙት ነገር ነው ። ሙት ነገር የነኩት ሁሉ አብረው ይሞታሉ ። በብሉይ ኪዳን ከታዘዙት ሥርዓቶች አንዱ በድን መንካት ያረክሳል የሚል ነው ። በአዲስ ኪዳን ግን በጥምቀት ጸጋን ያገኘ ፣ በሜሮን የከበረ ፣ ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ ፣ ታቦተ ሥላሴ ነውና የሰውን ሥጋ ወይም በድን ስመን እንሸኘዋለን ። ትንሣኤ ዘጉባዔን በማመን በተስፋ የክርስቲያንን በድን እንቀብረዋለን ። ትዕቢት የሞተ ነገር ነው ። የሚነካውን ሁሉ ያረክሳል ። ሰዎች ትዕቢት ሲጀምራቸው ውድቀት እያደባባቸው ነው ። የመዋረድ ዋዜማው ትዕቢት ነው ። ትዕቢት ከሆኑት በላይ ራስን አተልቆ ማየት ነው ። በዚህ ምክንያት ኃጢአት በዓለመ መላእክትና በዓለመ ሰብእ መካከል መግቢያ አገኘ ። ሳጥናኤልን ሰይጣን ያሰኘ ፣ አዲሱ ሰው የተባለውን አዳምን አሮጌ ሰው ያሰኘ ትዕቢት ነው ። በዚህ ምክንያት ትዕቢት ከአርእስተ ኃጣውዕ አንዱ ነው ። ትዕቢት በጣም ጥንቃቄ ካላደረግን በቶሎ የሚይዘን ነው ። ሰው እኔ እኮ አመንዝራ አይደለሁም ፣ እንደ እገሌም ሌባ አይደለሁም ካለ እውነት ቢሆን እንኳ ትዕቢት ነው ። ሰይጣን በሌሎች ነገሮች ካሸነፍነው በትዕቢት ደግሞ ይመጣብናል ። እኔ እኮ ትሑት ነኝ ብሎ መኩራትም እርሱ ትዕቢት ነው ።

ትሕትና በመካከል ያለ ነው ። ከመጠን በላይም ራስን ከፍ አለማድረግና ከመጠን በታች ራስን ዝቅ አለማድረግ እርሱ ትሕትና ነው ። ትሕትና የዝቅተኝነት ስሜት ሳይሆን በእግዚአብሔር የመታመን ጥበብ ነው ። የእግዚአብሔር ሰዎች ተለይተው የሚታወቁት በትሕትናቸው ነው ። ራስን በትክክል ማወቅ እርሱ ቅዱስነት ነው ። ጻድቁ አብርሃም፡- እኔ አፈርና አመድ ስሆን ከጌታዬ ጋር እናገር ዘንድ እነሆ አንድ ጊዜ ጀመርሁ” ብሏል ። /ዘፍ. 18፡27 ።/ አበ ብዙኃን የተባለው ፣ ሥላሴን በቤቱ በእንግድነት የተቀበለው ፣ ስለ ሰዶም ጥፋት የማለደው ፣ በዓለም ላይ ያሉ አይሁዶች ፣ ክርስቲያኖችና ሙስሊሞች አባታችን የሚሉት እርሱ እኔ አፈርና አመድ ነኝ አለ ። ትሕትና ራስን በእግዚአብሔር በማየት ሲገኝ ፣ ትዕቢት ደግሞ በጎረቤት ኑሮ ራስን በማየት ይመጣል ። አብርሃም በእግዚአብሔር ፊት እንደ ቆመ አውቋልና ፍጹም ትሑት ሆነ ። በእግዚአብሔር ፊት ስንቆም ራሳችን ያንስብናል ። ይህ ማነስም ክብርና ደስታ በውስጡ ያለው ነው ። ንጉሡ ዳዊትም፡- እኔ ግን ትል ነኝ ሰውም አይደለሁም የሰው ማላገጫ በሕዝብም ዘንድ የተናቅሁ ነኝአለ ። /መዝ. 21፡6 ።/ ዳዊት እስከ ዛሬ የተከበረ ንጉሥ ነው ። ጌታችንም ወልደ ዳዊት ተብሏልና ክብሩ ለዘላለም ነው ። ላለፉት ሦስት ሺህ ዓመታት ቤተ አይሁድ ፣ ላለፉት ሁለት ሺህ ዓመታት ቤተ ክርስቲያን የዳዊትን ዝማሬ በየቀኑ ይዘምራሉ ። ዳዊት ዝናው ያልፈዘዘው ፣ በየቀኑ የሚያበራው ትሑት ስለነበረ ነው ። ትዕቢተኞች ራሳቸውን ከፍ ስለሚያደርጉ የወደቁ ቀን የሚያነሣቸው የለም ። ትሑታን ግን ያለ ዘመናቸውም ይከብራሉ ። በቅዱሳን ስም የተሰየሙ አብያተ ክርስቲያናት የትሑታን ስምና ዝክራቸው እንደማይጠፋ ምስክር ናቸው ። ትዕቢተኞች የሠሩአቸው የራሳቸው ሐውልቶች ግን ፈርሰዋል ።
ሐዋርያው ጳውሎስም እኔ የኃጢአተኞች ዋና ፣ አውራ ፣ ፊት መሪ ፣ የበደለኞች በደለኛ ነኝ አለ ። ይህ ሐዋርያ የሰረቀ ፣ ያመነዘረ አልነበረም ። አዳኙን ክርስቶስን የገፋ ነበረ ። ሐዋርያው የኃጢአተኞች ዋና የነበረውን ሰይጣንን የእርሱን ወንበር ነጥቆ ፣ የኃጢአተኞች አውራ የነበረውን የአዳምን ስም ወስዶ ራሱን እጅግ ኃጢአተኛ አድርጎ ያቀርባል ። ሐዋርያው ራሱን ኃጢአተኛ ነኝ የሚለው ጻድቅ እንዲሉት አይደለም ። እኛ “እኔ ኃጢአተኛ ነኝ” የምንለው ጻድቅ እንዲሉን ፣ “እናንተማ እንዲህ ካላችሁ እኛ ምን እንበል ?” እንዲሉን ነው ። እውነተኛ ትሕትና ራስን ኃጢአተኛ ማለት ሳይሆን ኃጢአተኛ ሲሉን መታገሥ ነው ይባላል ።
የሃይማኖታችን ራስና ሊቀ ካህናት የሆነው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም “እኔ የዋህና በልቤም ትሑት ነኝ” ብሎናል ። /ማቴ. 11፡28-30 ።/ የጌታችን ትሕትና ኃጢአተኞች ላይ በቃል ፍርድ ፣ በልብም ትዝብት የሌለው ስለሆነ ነው ። በሌሎች ድካም ላይ በቃል መፍረድ ፣ በልብ መታዘብ እርሱ ትዕቢት ይባላል ። ጌታችን ግን በልብ ትሑት ነበረ ። በአንገት ሰበር ፣ በጉልበት ሸብረክ በማለት ብዙዎች ትሑታን ናቸው ። በፊት ለፊት ቅዱስ አባታችን እያሉ በስተኋላ ሳይበቁ ቅዱስ የሚሉ አያሌ ናቸው ። ትሕትና የልብ ሲሆን እውነተኛ ነው ።
ታዲያ ዛሬ ያለው ክርስትና አብነት ያደረገው ማንን ይሆን ? ትዕቢት ፣ በሌሎች መፍረድ ፣ ጭካኔ ፣ ጉረኝነት ፣ ወንድነት ፣ ፉከራ ፣ እኔ እኔ ማለት ከማን የወረሰው ይሆን ? የራሳችንን ምስጋና ቁጭ ብለን በፈገግታ የምንሰማው ፣ ሌሎችን እያሳነስን ስለ ራሳችን ካብ የምንክበው ከማን አግኝተነው ነው ? ክርስትና ከፈገግታ ይልቅ ልባዊ ፍቅር ፣ ከጥርስ ይልቅ ውስጣዊ ንጹሕነት ፣ ከልብስ ይልቅ ጸጋ እግዚአብሔር ፣ ከብዙ ንግግር ይልቅ ጥቂት ተግባር ይፈልጋል ። ሐዋርያው ጴጥሮስ፡- ብርና ወርቅ የለኝም፤ ይህን ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ ፤ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሣና ተመላለስ” በማለት ሽባውን ተረተረው ። /የሐዋ. 3፡6 ።/ ዛሬ ብዙ ርስት ፣ ብዙ ብርና ወርቅ አለን ። ጴጥሮስ ግን ብርና ወርቅ የለውም ፤ ፈውስ ግን አለው ። እኛ ብርና ወርቅ አለን ፣ ፈውስ ግን የለንም ። ልዩነታችን እዚህ ላይ ነው ።
የእግዚአብሔር ቸርነትና ምሕረት በትክክል ቢነገር ብዙ ሰዎች ንስሐ ይገቡ ነበር ። ንስሐ የሚገቡ ሰዎች የጠፉት የእግዚአብሔር ቸርነት ፣ የጌታችን ማዳን ስላልተነገረ ነው ። ብዙ ኃጢአተኞች በዐውደ ምሕረት ስንሰዳደብ ፣ በዘመናዊ መገናኛዎች ስም ስንጠፋፋ ፣ የእገሌ መረጃ አለኝ ስንል እየሰሙንና እያዩን ፍጹም ከክርስትና ርቀዋል ። ዛሬ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተደበቁ ጨካኞች በዓለም ቢፈለጉ አይገኙም ። ሰይጣን ሥራው ከቤተ ክርስቲያን ማስወጣት ብቻ አይደለም ። ወደ ቤተ ክርስቲያንም የሚያስገባቸው ሰዎች አሉ ። መንጋውን እንዲበጠብጡ ፣ ሰዎች ተስፋ ቆርጠው እንዲጠፉ የሚያደርጉ የሰይጣን የውስጥ ካድሬዎች አሉ ።
ቤተ ክርስቲያን ኃጢአተኞች በክርስቶስ ደም ታጥበው የሚነጹባት ቤተ ሕሙማን እንጂ ቤተ ፍጹማን አይደለችም ። ዓለሙ ጻድቅ ቢሆን ኑሮ የእግዚአብሔር ልጅ የሰው ልጅ መሆን ባላስፈለገው ነበር ። የሰዎችን ስህተት እንድንሸፍን እንጂ እያስፈራራን ገንዘብ እንድንቀበል አልተጠራንም ። ይህን ክፋት በዓለም ያሉም ገና አልደረሱበትም ። ክርስቶስ ግን የመጣው ለኃጢአተኞች ነው ። ኃጢአተኞችን ስንገፋ የወልደ እግዚአብሔርን ደም ከንቱ እናደርገዋለን ። እርሱ ኃጢአትን ይጠላል ፣ ኃጢአተኞችን ይወዳል ።እኛ ደግሞ በተቃራኒው ኃጢአተኞችን እንጠላለን ፣ ኃጢአትን እንወዳለን ።
ሐዋርያው ጳውሎስ እየተናገረ ያለው የኃጢአተኞች ዋና በምሆን በእኔ ላይ ምሕረቱን ያበዛው ጳውሎስን ይቅር ያለ እኛንማ ይቅር ይለናል ብለው ኃጢአተኞች ተስፋ እንዲያደርጉ ነው ይላል ። ትልቁን ከማረ ትንሹን መማሩ እርግጥ ነው እያለ ነው ።
ጌታችን የመጣው ኃጢአተኞችን አድራሻ አድርጎ ነውና ውስጣዊ ክስ የሚሰማችሁ ፣ በራሳችሁ ፊት መቆም ያቃታችሁ ፣ ራሳችሁን በጸጸት የምትቀጡ ወደ መድኃኒታችሁ በንስሐ ቅረቡ ። በፊቱ ስትወድቁ ያለፈው ዘመን ታሪካችሁ አብሮ ይወድቅና አዲሱን ሸክም ፍቅርን ይዛችሁ ትነሣላችሁ ። ሸክም አስጥሎ ሸክም የሚሰጥ ፣ የሚከብደውን ጭነት አውርዶ ፣ ቀሊል ቀንበር የሚያሸክም ፣ የሚበልጠውን ሸክም ወስዶ የሚያስደስተውን ኃላፊነት የሚሰጥ ጌታ እየጠበቃችሁ ነው ። መዳን ኃላፊነት መሆኑን ጨምሮ ሊነግራችሁ ነው ።
ጌታችን ኃጢአተኞችን ሊያድን መምጣቱ የታመነና ሁሉ ሊቀበሉት የሚገባ መሆኑን ይናገራል ። እኔ ይቅር አልባልም የሚል ስጋት ያለባቸው ሰዎች አሉ  ። የራሳቸውን ስርየት ተቀብለው ሌሎች ይቅር እንደሚባሉ የማይቀበሉም አሉና ይህን አለ ።
የኃጢአተኞችና የቀራጮች ወዳጅ ተብለህ በእኛ ምክንያት ሐሜት የተቀበልህ ጌታችን ምስጋና ለስምህ ይሁን ።
1ጢሞቴዎስ /17/
ኅዳር 25 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም