የትምህርቱ ርዕስ | የቀደመው ታሪኬ

“አስቀድሞ ተሳዳቢና አሳዳጅ አንገላችም ምንም ብሆን፥ ይህን አደረገልኝ፤ ነገር ግን ሳላውቅ ባለማመን ስላደረግሁት ምሕረትን አገኘሁ” /ጢሞ. 1፡13 ።/
የእግዚአብሔር ሰዎች ስላለፈው የውድቀት ታሪካቸው መናገር አያሳፍራቸውም ። ምክንያቱም በእግዚአብሔር ምሕረት አግኝቷልና ። ስለ ቀደመው ሕይወታቸው የሚያወሩት ናፍቆአቸው ፣ ኮርተውበት አሊያም ተሳቅቀው ሳይሆን የእግዚአብሔርን ፍቅር ለዓለም ለመዘከር ነው ። እግዚአብሔር ጻድቃን ቢላቸውም እነርሱ ግን ራሳቸውን ኃጢአተኛ ብለው ይጠሩት ነበር ። የእግዚአብሔር ከፍታ በታያቸው ቊጥር ራሳቸው ያንስባቸው ነበር ። ለሕይወት ሁለት ዓይነት ገጽ ወይም መልክ የሚሰጥ እግዚአብሔር ብቻ ነው ። ቀድሞ ሙት ነበርሁ ለማለት ሕይወትን ማግኘት ያስፈልጋል ። ጨለማ በታሪክ መልክ የሚወራው ብርሃን ሲገኝ ብቻ ነው ። የጠዋቱ ብርሃን የእኛ እጅ የሌለበት የእግዚአብሔር የፍቅር ስጦታ ነው ። የሕይወት ብርሃንም የእግዚአብሔር ስጦታ ነው ። የተሰረዘ ታሪክ ቢሆንም ሐዋርያው ግን ያለፈውን ዘመን ውድቀቱን እያነሣ የእግዚአብሔርን ምሕረት ያውጅበታል ። እኔ የጀመርሁት ከዚህ ሳይሆን እኔ የጀመርሁት ከዚያ ነው ይላል ። ብዙ ሰው እንዳለ ያለ አድርጎ ራሱን ለመግለጥ ይፈልጋል ። ቀድሞም ቢሆን እንደ ዛሬው አማኒ ፣ እንደ ዛሬው ጤነኛ ፣ እንደ ዛሬው አገልጋይ ፣ እንደ ዛሬው ባለጠጋ እንደሆነ ለመናገር ይዳዳዋል ። “የትላንት ታሪክ የሌለው ጻድቅ ግን የለም ።” የእግዚአብሔር አዳኝነት ያስፈለገውም የሰው ውድቀት ስላለ ነው ።

የእግዚአብሔር ሰዎች የማይፈሩት ሁለተኛው ነገር የሚባሉትን ለመስማት ነው ። የሚባሉት ላይ አይዘገዩም እንጂ ለመስማት ደፋር ናቸው ። ስማቸውን ጥለው በክርስቶስ ክርስቲያን ተብለዋል ። ስለዚህ ስለ ስማቸው አይጨነቁም ። ዓለም ሳይጥለው ቀድመው ጥለውታል ። በምርጫቸው አያጨማልቁት እንጂ ሰዎች በጥላቻ ጥላሸት ቢቀቡአቸው አይጨነቁም ። ሰዎች የሚሏቸውን ክርስቶስ ስለማይላቸው በዚህ ደስተኞች ናቸው ። የሰዎች ስም መስጠት የመጨረሻው ብያኔ አይደለም ። ደግሞም ውሉደ እግዚአብሔር ተብለዋልና የእገሌ ልጅ ተብለው የሚጠሩበት ስም ባይኖራቸው አይጨነቁም ። ትልቁም ትንሹም ማጠቃለያው መቃብር ነው ። የእግዚአብሔር ልጅ መሆን ግን የማያልፈውን ዓለም መውረስ ነው ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊልጶስ ቂሣሪያ፡- ሰዎች የሰውን ልጅ ማን እንደ ሆነ ይሉታል ? ብሎ ጠየቀ ።”/ማቴ. 16 ፡ 13 ።/ ሰዎች የሚሉንን ለመስማት ድፍረት እንዲኖረን እያስተማረን ነው ። ሰዎች ክርስቶስን የሚሉት እንኳ አላጡም ። የሆነውን ሳይሆን ያልሆነውን ተናገሩ ። ክርስቶስ ማን እንደሆነ የነበራቸው እውቀት ሳይሆን ግምት ነበር ። ግምታቸውን ግን እንደ እውቀት በድፍረት ይናገሩት ነበር ። ሰዎች የሚሰጡት ክፉ ስያሜ ብቻ ሳይሆን መልካም ስያሜም ትክክል አይደለም ። ይኸውም ጌታችንን፡- አንዳንዱ መጥምቁ ዮሐንስ ፥ ሌሎችም ኤልያስ ፥ ሌሎችም ኤርምያስ ወይም ከነቢያት አንዱ ነው” ይሉት ነበር ። እርሱ ግን ወልደ አብ ፣ ወልደ ማርያም ነበረ ። ሰዎች ክፉ ሲናገሩብንም ሆነ መልካም ሲናገሩልን ሁለቱንም በማስተዋል ተቀብለን ማዘንም ሆነ መዝለል የለብንም ። እኛ የሆነውን ብቻ ነን ። መልካም ብንሆን ለእግዚአብሔር ደስታ ነው ፤ ክፉ ብንሆንም የሚያድነን እርሱ ነው ።
ሐዋርያው፡- “አስቀድሞ”በማለት ይናገራል ። አስቀድሞ ክፉ ታሪክ ነበረው ። ትላንቱ የሚያጸጽት ገጽታ ነበረው ። እርሱ አስቀድሞ ተሳዳቢና አሳዳጅ አንገላች ነበረ ። ክፉ ነገርን በነበር ለመተረክ በቅቷል ። አስቀድሞ ነበረ ፣ ዛሬ ግን አይደለም ። የጻፍነው እኛ ብንሆን በአሁን ሰዓት ተሳዳቢና አሳዳጅ አንገላችም ነኝ እንል ነበር ። ክፋት ታሪክ ሳይሆን ሕያው ሁኖብናልና ። ሐዋርያው ጳውሎስ ተሳዳቢ ነበርሁ እያለ ነው ። ሥጋዊ ቅንዓት ይዘን ለሃይማኖት ዘብ ስንቆም የመጀመሪያው መሣሪያችን ስድብ ነው ። ስድብ የምንጠላውን ሁሉ ማጠልሸት ነው ። ስድብ ሕግ የለውምና የተገኘውን ጭቃ መለጠፍ ነው ። ስድብ ከሐሜት ልዩ የሚያደርገው ሐሜት ሰውዬው በሌለበት ፈርቶ ክፉ መናገር ሲሆን ስድብ ግን ሰውዬው ባለበት ደፍሮ ክፉ መናገር ነው ። ስድብ ለእጅና ለእግር የሚወረወር ሳይሆን ስድብ ለኅሊና የሚወረወር ቀስት ነው ። የታሰረ ኅሊና የተፈቱ እግሮች ቢኖሩትም መራመድ አይችልም ። ስድብ ሰውዬውን በሆነውና ባልሆነው ነገር ማዋረድና ተስፋ የለሽ ማድረግ ነው ። ስድብ የሰይጣን ዋነኛ መሣሪያው ነው ። ስድብ በሰብእና ላይ የሚወረወር ጦር ነው ። ስድብ ከአንደበት ኃጢአቶች ዋነኛው ነው ። ስድብም ሰውየው መቆም እንዳይችል የማሽመድመድ ዘዴ ነው ። ሐዋርያው እንዲህ ነበርሁ እያለ ነው ። የሚሳደበው ደግሞ ወንጌልንና ወንጌላውያንን በመሆኑ ትልቅ ውድቀት ውስጥ ነበር ።
አሳዳጅ ነበርሁ ይላል ። ማሳደድ ሁለት ዓይነት ነው ። የመጀመሪያው ከሰፈሩ ፣ ከቀዬው ፣ ከቤቱና ከቤተሰቡ ተለይቶ እንዲባረር ፣ በኃይል እንዲወጣ ማድረግ ነው ። ሁለተኛው በሐሜትና በውግዘት ከሰው ኅሊና እንዲወጣ ማድረግ ነው ። ቢናገር እንደ እብድ እንዲቆጠር ፣ ቢያስተምር እንደ መናፍቅ እንዲታይ ማድረግ ነው ። ሐዋርያው በሁለቱም ስልት ሳይንቀሳቀስ አልቀረም ።
አንገላችም ነበርሁ ይላል ። ከሮማው ፍርድ ቤት የመግደል ፣ ከአይሁድ ሸንጎ የማግለል ሥልጣን አግኝቶ በአገር ውስጥና በውጭ አገር የነበሩትን ክርስቲያኖች ያሳድድና ያንገላታ ነበር ። ማሳደድ ማባረር ሲሆን ፣ ማንገላታት ግን በወኅኒ እንዲጣሉ ፣ እንዲገረፉና እንዲወገሩ ማድረግ ነው ። ሐዋርያው እጅግ የጠላው ክርስትና እጅግ ወረሰው ። ክርስትና ጠላትን ወዳጅ የማድረግ ፣ አሳዳጁን ተሰዳጅ የማድረግ ብቃት አላት ። ሰዎች በጣም ሲቃወሙ በጣም ሊድኑ ተቃርበዋል ። መፍራት ልዝቦቹን ነው ። የከረረ መበጠሱ አይቀርም ። 
ሐዋርያው፡- “አስቀድሞ ተሳዳቢና አሳዳጅ አንገላችም ምንም ብሆን፥ ይህን አደረገልኝ፤ ነገር ግን ሳላውቅ ባለማመን ስላደረግሁት ምሕረትን አገኘሁ” ይላል ። ሳላውቅ ፣ ባለማመን ስላደረግሁት ይላል ። ሐዋርያው የአይሁድ ሃይማኖት መምህር ነበረ ። ብዙ ዘመኑንም በመማር ያሳለፈ ፣ ስመ ጥሩ ከሆነው ከገማልያል እግር ሥር ተቀምጦ የተማረ ፣ በአይሁድ ሸንጎም አባል የሆነ ፣ የተከበረ ሰው ነበር ። ነገር ግን ባለ ማወቅ ስላደረግሁት አለ ። ጌታችንም የሰቀሉትን እነዚያን የሃይማኖት ምሁራን፡- “አባት ሆይ፣ የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው” አለ ። እኛ ይቅር ለማለት የምንቸገረው የሚያደርጉትን ያውቃሉ ብለን ነው ። መጻሕፍትን ቢያውቁም የሚያደርጉትን አያውቁም ። ሐዋርያው ባለማመን ስላደረግሁት ይላል ። ሐዋርያው ክርስትናን ያሳድድ የነበረው ለኦሪት እምነቱ ቀንቶ ነው ። አሁን ግን አላምንም ነበር እያለ ነው ። አላውቅም ፣ አላምንም ነበር ማለት ትልቅ ትሕትና የሚጠይቅ ነው ። ማንም ሰው ከዜሮ መጀመር አይፈልግም ። ባለው ላይ መደመር ይፈልጋል ። ሐዋርያው ግን በእግዚአብሔር ምሕረት ስለተከለለ ይህን አለ ። እግዚአብሔር ይቅር ካለን የሚቀርብን ጸጋ የለም ።
ምሕረት አገኘሁ ይላል ። በብዙ አገሮች ይቅርታና ምሕረት በመንግሥት ደረጃ ይሰጣል ። ፍርዱ በሕግ ስለሆነ ምሕረትና ይቅርታም በሕግ መሆን አለበት ። ሕጋዊ ያልሆነ ምሕረት ሕጋዊውን ፍርድ መሻር አይችልም ። ይቅርታ የሚባለው በአብዛኛው ተሳስተናልና ቅጣት ይቅለልልን የሚሉ እስረኞች የሚቀበሉት መፈታት ነው ። ምሕረት ግን መንግሥት ራሱ የቅጣት ዘመናቸውን አስቦ የሚለቃቸው እስረኞች የሚያገኙት  ነጻነት ነው ።አሊያም ይቅርታ የእስረኛው ጥያቄ ሲሆን ምሕረት የመንግሥት ምላሽ ይሆናል ። ሐዋርያው ምሕረት አገኘሁ ሲል እኔ ስገፋው እግዚአብሔር ግን አብዝቶ ቀረበኝ ፣ ሞት ሲገባኝ ሕይወትን ፣ እስር ሲገባኝ አገልግሎትን ሰጠኝ እያለ ነው ። ሐዋርያው የእግዚአብሔር ምሕረት መንገድ ዘግቶ ባይመልሰው ፣ እጆቹ በደማስቆ ክርስቲያኖች ደም ይጨቀዩ ነበር ። ትልቁን ክፋቱን ሳይጨርሰው እግዚአብሔር አቋረጠው ። እኛም ወደ እግዚአብሔር የተመለስነው ይበልጥ እግዚአብሔርን ለማሳዘን በተነሣንበት ጊዜ ይሆናል ። የክፋት መንገዳችንን ሳንጨርሰው ገንዘቡ ያደረገን እንዴት ቡሩክ ነው !
ሐዋርያው የሕግ አስተማሪ ሊሆኑ ለሚሹት ሰዎች እኔ ተሳዳቢና አሳዳጅ ፣ አንገላችም ሳለሁ ሐዋርያ የሆንሁት በቸርነቱ ነው እያላቸው ነው ። በምሕረት ገብተው በሕግ ለመኖር ለሚያስቡ ፣ ለሚመጻደቁ ፣ ሌሎችንም ለሚንቁ ፣ የትላንቱን ለረሱት እያስታወሰ ነው ። እግዚአብሔር ቀጣዩ መንገድ እንዳይጠፋን የመጣንበትን መንገድ ያስታውሰናል ።
በእውነት ጌታዬ ሆይ ማደሪያህ ይባረክ !
1ጢሞቴዎስ /15/
ኅዳር 20 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም