የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ

የዲያቆን አሸናፊ መኰንን ገጽ 

አገልግሎቱ ባለቤት አለው

 “ለአገልግሎቱ ሾሞኝ ታማኝ አድርጎ ስለ ቈጠረኝ፥ ኃይል የሰጠኝን ክርስቶስ ኢየሱስን ጌታችንን አመሰግናለሁ” 1ጢሞ. 1፡12
አገልግሎት የአገልጋዮች ሳይሆን አገልግሎት የእግዚአብሔር ነው ። አገልግሎት የእግዚአብሔር ነውና ለአገልጋዮች ብቻ የምንተወው አይደለም ።አገልግሎት የእግዚአብሔር ነውና በአገልጋዮች ማንነት የምንመዝነው አይደለም ። አገልግሎት የእግዚአብሔር ነውና ዋጋ ከፋዩ ሰማያዊ አምላክ ብቻ ነው ። አገልግሎት የእግዚአብሔር ነውና ማንም ሊያቆመው አይችልም ። አገልግሎት የእግዚአብሔር ነውና አንድ ቀን ሂሳብ ይተሳሰበናል ። ሐዋርያው ጳውሎስ እንደ እኛ አገልግሎቴ አላለም ። “አገልግሎቱ” አለ እንጂ ። እኛ አገልግሎቴ ስንል እንደ አራስ ነብር ስንቱ በቊጣ አሳደድነው ። እኛ አገልግሎቴ ስንል ስንቱን ገድለን ለመኖር አቀድን ። እኛ አገልግሎቴ ስንል ወንድማችንን እየጠላን እግዚአብሔርን እንወዳለን አለን ። እኛ አገልግሎቴ ስንል ስንቱን በቁም ለመቅበር ተነሣን ።

አገልግሎቴ የሚሉ ክልሌ እያሉ እንደሚፋጁ በግዛታቸው ለገባው ምሕረት የላቸውም ። አገልግሎቴ የሚሉ ቀረጥ የማይከፍሉበት ሱቃቸው አድርገው ስለሚመለከቱት ሌላውን አገልጋይ እንደ ደመኛ ያዩታል ። አገልግሎቴ የሚሉ ምእመኑን እንደ ደንበኛቸው ሲያዩ አገልጋዩን ደግሞ እንደ ተቃዋሚ ያዩታል ። ለዘመናት መነኩሴ ለመነኩሴ ፣ ቄስ ለቄስ ያግዛል እየተባለ ይተች ነበር ። የእኛ ደግሞ እኛን የሚመስለውን ካላጠፋሁ የሚል መሆኑ የሚገርም ነው ።
ሐዋርያው ጳውሎስ ስለ አገልግሎቱ ለመናገር የፈለገው ለምንድነው ? ብለን መጠየቃችን አይቀርም ። ከላይ የሕግ አስተማሪዎች ሊሆኑ የሚወዱ የሕጉን ምንነት ያልተረዱ ፣ ሕጉ ወንጀል ባለበት ብቻ ድምፅ እንዳለው ያላስተዋሉ ሰዎችን ሲመክር ቆይቷልና አሁን ደግሞ እርሱ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የተጨመረበትን ምሥጢር ማለትም የቸርነቱን መንገድ መናገር ፈለገ ። ሐዋርያው ጳውሎስ እንደ ሕጉ የገደለ ወይም ከገዳዮች ጋር የተባበረ ነውና የሚገባው ሞት ነው ። እንደ ቸርነቱ ግን የእግዚአብሔር አገልጋይ ሁኗል ። የኤፌሶን ሰዎችም በጸጋው ተጠርተው በሕግ ለመኖር ፈለጉ ። ሕጉን መፈጸም ሳይሆን በበጎነታቸው እንደ ተጠሩ ለማሰብ ሞከሩ ። ሐዋርያው ግን እኔ ራሴን በአገልግሎቱ ያገኘሁት በቸርነቱ ነው እያለ ነው ።አንዳንዱ ጥሩ አስተዳደጉን እያነሣ ፣ ሌላውም ጨዋነቱን ከግምት ውስጥ እያስገባ እግዚአብሔር በዚህ ብቻ እንዳዳነው ያስብ ይሆናል ፤ ሐዋርያው ግን ከቸርነቱ ውጭ አለኝ የምለው ምንም ነገር የለኝም እያለ ነው ።
“ለአገልግሎቱ ሾሞኝ ታማኝ አድርጎ ስለ ቈጠረኝ፥ ኃይል የሰጠኝን ክርስቶስ ኢየሱስን ጌታችንን አመሰግናለሁ” ይላል ። ሹመት ሹዋሚ አለው ። አገልግሎት ከፊት ሹመት ፣ ከኋላ ሽልማት አለው ። አገልግሎት ከፊት ሹመት ፣ ከኋላ ተጠያቂነት አለው ። ሐዋርያው አገልግሎትን ዕድል ብቻ ሳይሆን አደራም አድርጎ እየተመለከተው ነው ። አንድን አሳዳጅ ሰው ፣ ትልቁን ምስክር እስጢፋኖስን ያስገደለ ቀናተኛን ረቢ አገልጋይ ለማድረግ እኛ አናምነውም ። እግዚአብሔር ግን ጳውሎስን ታማኝ አድርጎ ቆጠረው ። እኛ በመጠራጠር ፣ እግዚአብሔር ግን ታማኝ አድርጎ በመጠር ይጠራል ።እግዚአብሔር የምንደሰትበት ብቻ ሳይሆን የሚደሰትብን መሆኑን ማሰብ እንዴት ደስ ይላል ። እግዚአብሔር የምናምነው ብቻ ሳይሆን ታማኝ አድርጎ የሚቆጥረን መሆኑን ማሰብ እንዴት ልብን ያሳርፋል ። እግዚአብሔር ትእዛዛቱን የሰጠን ስለሚያምነን ነው ። እኛ የማናምናቸውን አናዛቸውም ። እግዚአብሔር ግን ስለሚያምነን ያዘናል ። ትላንት እንዳልነገረን አድርጎ ዛሬም ይናገረናል ።
ትእዛዝ ለሁሉ ሲሰጥ ሹመት ግን ለሁሉ አይሰጥም ። ሁሉም ክርስቲያን አገልጋይ ነው ቢባልም ሁሉም ግን ሹመት ያለው አገልጋይ አይደለም ። ብዙ ጊዜ እኛ የንጉሥ ካህናት ነን የሚለውን ቃል በመጥቀስ አገልጋይ ወይም ካህን አያስፈልግም ይባላል ። ይህ ቃል ለመጀመሪያ ጊዜ የተነገረው እስራኤል ከግብጽ ከወጡ በኋላ በምድረ በዳ ላይ ነው ።እናንተም የካህናት መንግሥት የተቀደሰም ሕዝብ ትሆኑልኛላችሁ ።” ይላል /ዘጸ. 19፡6/ ። በዚህ ቃል መሠረት እስራኤል ሁሉ የንጉሥ ካህናት ናቸው ። በዘጸ. 28፡1 ላይ ደግሞ፡- አንተም ወንድምህን አሮንን ከእርሱም ጋር ልጆቹን ከእስራኤል ልጆች መካከል ለይተህ ካህናት ይሆኑልኝ ዘንድ ወደ አንተ አቅርብ ይላል ። መላው እስራኤል የካህናት መንግሥት ናቸው ። ምክንያቱም ተዋጅተው ከግብጽ ወጥተዋልና አሮንና ልጆቹ ግን የተሾሙ ካህናት ናቸው ። በአዲስ ኪዳንም ተዋጅተው የወጡ ምእመናን በሙሉ ካህናት ሲባሉ እንደ ጳውሎስ ያሉት ደግሞ የተሾሙ ናቸው ። /1ጴጥ. 2፡9፤ ሉቃ. 10፡1/ ። ስለዚህ የእግዚአብሔርን ደጅ የሚከፍቱና የሚዘጉ ካህናት ወይም አገልጋዮች አያስፈልጉም ብለን ማሰብ የለብንም ። ካህን ማለት ኮሄን ከሚል የዕብራይስጥ ቃል የወጣ ሲሆን አገልጋይ ማለት ነው ።
ጥሪ ፣ ሹመት ፣ ተልእኮ ፣ አገልግሎት የሚባሉ አራት ነገሮች አሉ ። የክርስቲያንነትና የአገልግሎት ጥሪ የሚባል ሁለት ዓይነት ጥሪ አለ ። ሹመት ደግሞ ከጌታችን በቀጥታ የምንቀበለው ወይም ሐዋርያዊ መስመር ያለው ተዋረድ ፣ ዐሠረ ክህነት ነው ። ተልእኮ ወንጌልን ለማዳረስ የምንወጣበት የዘመቻ ሥራ ነው ። አገልግሎት ደግሞ የተተከለውን የምናሳድግበት እረኝነትና አስተማሪነት ነው ። ሐዋርያው ጳውሎስ ስለ ጥሪውና ሹመቱ ይናገራል ። እነዚህ በአንድ ጊዜ የሚከናወኑ ናቸውና ።
እግዚአብሔር ከትእዛዙና ከሹመቱ ጋር ማስፈጸሚያ እንዲሆን ኃይል ይሰጣል ። መንግሥት ሹመት ለሰጠው ሰው ኃይል አብሮ ይመድባል ። ኃይል ባይኖር ሹመት ከንቱ ይሆን ነበር ። እግዚአብሔርም ከሹመቱ ጋር ኃይል የሚሰጠው ራሳችንን እንድንገዛና አገልግሎቱን እንድናከናውን ነው ። ያለ እግዚአብሔር ኃይል ራሳችን መግዛት አይቻልም ። የእግዚአብሔር ትእዛዝም ሌጣ ሳይሆን በትኩስነት ለሚታዘዙት ኃይል የተሞላ ነው ። ስንዘገይ ግን ኃይሉ ይሄድና ትእዛዙ ይቀራል ። ማገልገልም የሚታይና የማይታይ ፈተና ያለበት ነው ። ሰዎችን ከአጋንንት እስር ቤት ማስወጣት ነው ። ያሰራቸው እንዲሁ አይመለከተንም ። ይታኮሳል ፣ ይጋደላል ። ማገልገል ሰዎችን ከሲዖል እሳት ማውጣት ነው ። ሲዖልን ከሚያህል እቶን ነፍስ ሲያመላልሱ ወላፈኑ አይንካኝ ማለት የሚገርም ነው ። ሰዎችን ለራሳቸው መዳን ደጅ መጥናት ነውና አገልግሎት የእግዚአብሔር ኃይል ያስፈልገዋል ።
“ኃይል የሰጠኝን ክርስቶስ ኢየሱስን ጌታችንን አመሰግናለሁ” ይላል ። መሾሙ አደራ መስጠት ሲሆን ኃይል መስጠቱ ደግሞ የአብሮነቱ ምስክር ነው ። አንድ ሹም ኃይል አብሮት ካለ የሾመው አብሮት እንዳለ ይረዳል ። ሐዋርያው ጳውሎስም የእግዚአብሔር ኃይል አብሮት እንዳለ ተረድቷል ። ስለዚህም ያመሰግናል ። ያ ኃይል የሚሠራው ነገር አለ፡-
1-  የሐዋርያውን ሕይወት ከሚታይና ከማይታይ አደጋ ይጠብቃል ።

2-  የሐዋርያው የሆኑትን ሁሉ ነቅቶ ይጠብቃል ።

3-  የአጋንንትን ግዛት እየጣሰ ምርኮን ለሐዋርያው ያሰናዳል ።

4-  ሐዋርያው ለጆሮ ሲናገር ያ ኃይል ደግሞ ለልባቸው እየተናገረ ቃሉን ያትማል። 

5-  በክፉ ነገሮች ላይ ፈውስን ይሰጠዋል ። ደዌያትንና አጋንንትን ይገሥጻል ።

6-  በማዕበልና በወጀብ ውስጥ ሲያልፍ ሐዋርያውን ያጽናናዋል ።

7-  ለሰማዕትነት እንዲጨክን በማድረግ ለክብር ያበቃዋል ።
እግዚአብሔር ተራ ጥሪ አልጠራንም ። ሹመቱም ኃይል አልባ አይደለም ። ስለዚህ ማስተዋል ያለብን ነገሮች አሉ ። የማናየውንና የማንሰማውን የሚያይና የሚሰማልን አምላክ አለን ። እኛን ብቻ ሳይሆን የእኛ የሆኑትም የደኅንነት ዋስትና አላቸው ። ፊታውራሪ ሁኖ እየቀደመ ድልን የሚያዘጋጅልን የአገልግሎቱ አምላክ አብሮን አለ ። የሰዎችን ልብ እያሰናዳ ፍሬ ያበዛልናል ። በክፉ ነገሮች ላይ ሥልጣን ሰጥቶናል ። ፈተናና መከራ ቢበዛም ድሉ የታወቀ ጦርነት ነው ። በመጨረሻም በሞቱ እንመስለው ዘንድ ለሰማዕትነት ያግዘናል ።
እግዚአብሔር አገልግሎቱን እኛ ላይ ጥሎት የሄደ ከመሰለን እግዚአብሔር ሥራውን የማይስት አምላክ ነው ። በመከራና በፈተና ውስጥ አሻግረን የእርሱን ተስፋ መስማት ቢያቅተንም የጠራን ግን ታማኝ ነው ። ስለዚህ መበርታት አለብን ። የአገልግሎቱ ጥሪና ሹመት እንዳለን ግን ማረጋገጥ መልካም ነው ። እንኳን እኔ እነ እገሌም ሰብከውታል ብለን የገባንበት ከሆነ ደግመን ማሰብ አስፈላጊ ነው ። ለአገልግሎት የሚያስፈልገው ወንድነት ፣ ሥጋዊ ጀግንነት ፣ ዲግሪና ቁመት አይደለም ። ጥሪና ጸጋ ነው ። ጥሪ የሌለው ሰው ጥሪ ያላቸውን ያፈናቅላል ። ጥሪዬ ምንድነው ? ብሎ መጠየቅ ተገቢ ነው ።
እስከ ዛሬ በቤትህ ለመቆየት ኃይል የሰጠኸን ጌታ ተመስገን !!
1ጢሞቴዎስ /14/
ኅዳር 19 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲ.አ.መ.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ
አዳዲስ መጻሕፍትን ይግዙ

ተዛማጅ ጽሑፎች

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ