የትምህርቱ ርዕስ | ማነው የሚያድነን ?

“መድኃኒታችን እግዚአብሔር” 1ጢሞ. 1፡1
እግዚአብሔር ለዘመናት በአዳኝነቱ ምሥጢር ሲገለጥ ኑሯል ። የሰው ልጆች ከበደል በኋላ ብዙ ዓይነት አደጋ እየተጋፈጡ ስለሆነ አዳኝ አስፈልጓቸዋል ። አዳም ከሞት የሚያድን አምላክ ከመፈለጉ በፊት ከሐፍረትና ከፍርሃት የሚያድን መድኃኒት ሽቷል ። አዳምና ሔዋን በበደል እኩል ቢሆኑም እርስ በርሳቸው ተፋፍረዋል ። በደል ከኅሊና ፊትም ስደተኛ ያደርጋል ። እግዚአብሔር ከሐፍረትም ያድናል ። ማፈር በሰውና በእግዚአብሔር ፊት መቆም አለመቻል ነው ። ከዚህ ሊያድን የሚችል እግዚአብሔር ብቻ ነው ። የሚያድንበት መንገድም በንስሐ ሲሆን የመቆም ብቃቱም የእርሱ ምሕረት ነው ። ሰዎች በሰዎች ፊት በድርቅና በመቆም ሐፍረትን ሊያሸንፉ ይችላሉ ።”የሌባ ዓይነ ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ” እንዲሉ ። ሰው ግን በእግዚአብሔር ፊት የሚቆመው በእግዚአብሔር ምሕረት ተሸፍኖ ብቻ ነው ። የተራቆተ ሰው በሰው ፊት ለመቆም ይቸገራል ። በነፍሱ ሐፍረት የሚሰማው ደግሞ በኅሊናውና በእግዚአብሔር ፊት መቆም ያቅተዋል ። አንድ ንጉሥ በምሕረት የለቀቀው ወንጀለኛ ያልበደለ ያህል በነጻነት እንደሚወጣ እግዚአብሔር ይቅር ያለውም በኅሊና ሰላም ይንቀሳቀሳል ። ሰው ራሱን ፣ ሰው ጎረቤቱንና እግዚአብሔርን ያፍራል ። ከዚህ የሚያድነው ግን እግዚአብሔር ነው ። እግዚአብሔር ከሐፍረት ያድናል ።

አዳምና ሔዋን በበደል በወደቁ ጊዜ ፍርሃት መጣባቸው ። ከዚህ በፊት የማያውቁት ስሜት ቢሆንም አሁን ተጫናቸው ። ፈርተው የማያውቁ ፈሩ ፣ በድለው የማያውቁ በድለዋልና በዚህ ቀን ብዙ ክፉ ነገሮችን አወቁ ። እግዚአብሔር ያዘዛቸው ከክፉ እውቀት ሊጠብቃቸው ነው ። ክፉን በትምህርት እንጂ በኑሮ ማወቅ ከባድ ነው ። ፍርሃት ኃጢአት የሚያስከትለውም የኅሊና ስቃይ ነው ። ፍርሃት ሁሉ ግን የሚመጣው በኃጢአት ነው ማለት አይደለም ። ፍርሃት የዓለም አስተዳዳሪ የነበረውን አዳምን በገነት ጫካዎች ውስጥ ደበቀው ። ፈፋ ውስጥ ፣ ገደል ውስጥ ተደብቀው ስለተያዙ ነገሥታትና የጦር አለቆች ብዙ ይወራል ። ያልፈራ ሰው ስለፈሪዎች የሚያወራው እየተዝናና ነው ። አዳም ትልቅ አስተዳዳሪ ቢሆንም በቅጠል ውስጥ ተሸሸገ ። ቅጠል ያመጣውን ፍርሃት ቅጠል አያርቀውም ። ዛሬም ሰዎች ፍርሃት ሲሰማቸው የተለያዩ ቅጠሎች ወይም ሱሶች ውስጥ ይደበቃሉ ። ከጠላት ዛቻ ፣ ከተፈጥሮና ሰው ሠራሽ አደጋ የተነሣ የሚመጣ ፍርሃት አለ ። ልቡናችን ተገንብቶ መቆም ሲያቅተው የሚመጣው ፍርሃት ካለመጸለይና ቃሉን ካለመሞላት የተነሣ የሚመጣ ነው ። ፍርሃትን የሚወልደው ጠባቂ ወታደር አለመኖር ፣ የከተማ ደጃፍ አለመዘጋት ፣ በሩ አለመቆለፉ አይደለም ። ይህ ሁሉ ባለበት ፍርሃት የሚንጣቸው ወገኖች አሌ የማይባሉ ናቸው ። “እባብ ያየ በልጥ ይደነብራል” እንዲሉ ያለፈው ክፉ ገጠመኝ ፈሪ አድርጎ ያስቀመጣቸው ብዙዎች ናቸው ። ሰይጣን ብዙ ሰዎችን ፈሪ አድርጓቸዋል ። ጠንቋይ የሚያፈቅሩ ከፍርሃት አይድኑም ። እግዚአብሔር ግን ከፍርሃት ያድናል ። ስለዚህ ሐዋርያው መድኃኒታችን ይለዋል ።
እግዚአብሔር ባለማዳን የሚያድናቸው ወገኖች አሉ ። አቤልን ሕይወቱ እንዳይጠፋ አላዳነውም ፣ ስሙ እንዳይጠፋ ግን አድኖታል ። እግዚአብሔር ለዘመናት የጽናት ምሳሌ የሚያደርጋቸው ሰዎች ባለ ማዳን ያዳናቸው ሰዎች ናቸው ። አቤል ወንድሙ ባይገድለውም ይሞት ነበር ። የማይቀረው ሞት ግን የክብር ስም ሁኖለት ይኸው የሰማዕታት ራስ ሁኖ ይኖራል ። እግዚአብሔር ዛሬም እኛን አስችሎ ሌሎችን ያስተምራል ። የእግዚአብሔር የአዳኝነቱ ምሥጢር እጅግ ረቂቅ ነው ። ይህም በይበልጥ የተገለጠው በጌታችን ሰው መሆን ነው ። አዳምና ሔዋንን በእባብ ሥጋ ተሰውሮ ጠላት እንዳሳታቸው ጌታችን ደግሞ የሰውን ሥጋ ለብሶ አድኗቸዋል ። ፍቅር ፣ ጥበብና እውነት በሌሉበት ማዳን ሊኖር አይችልም ።
ለእስራኤል እግዚአብሔር አዳኝነቱን የገለጠው ከፈርዖን ጋር ታግሎ ከግብጽ ሲያድናቸው ነው ። የእነርሱ የቅጣት ዘመን ሲጨርስ የፈርዖን የቅጣት ዘመን ይጀምር ነበር ። አጥፊና ጠፊው እየተገናኘ ቅጣት ይከናወናል ። እስራኤል የኤርትራን ባሕር የተሻገሩት በምሕረት ጥላ ስለሆኑ ነው ፣ ፈርዖን የሰጠመው በራሱ ጥላ ስለነበረ ነው ። እግዚአብሔር የሠራተኞች መብት ተሟጋች መሆኑን የምናውቀው እስራኤል ከግብጻውያን ወርቅና ብር እንዲበዘብዙ ባደረገ ጊዜ ነው ። ያ ወርቅና ብር በምድረ በዳ ላይ ደብተራ ኦሪት ወይም መቅደሱ የተሠራበት ነው ። እስራኤል እንዲያ ሳይረጋጉ አሥራት ማውጣታቸው በተረጋጋ ከተማ አሥራት የሚሰርቁትን ለማሳፈር ነው ።
እግዚአብሔር ከጠላት ያድናል ። እስራኤልን የገዙአቸው የሚጠሉአቸው ናቸው ። የሚጠሉን ሲገዙን ከባድ ነው ። እግዚአብሔር ግን የዘመናትን የባርነት ቀንበር ሰብሮ አዳናቸው ። ተፈጥሮን ሠራዊቱ አድርጎ እየተዋጋ ያዳናቸው እግዚአብሔር ነው ። እግዚአብሔር ሲዋጋ ሁሉም ነገር ይጣላናል ።
እግዚአብሔር የልቅሶ ዘመንን በድል ዝማሬ ለውጦ አገር አልባ የሆኑት እስራኤል ፣ አገር ያላቸውን ሕዝቦች ማስደንበር ጀመሩ ። የደረጀ ሠራዊት ያላቸውና የሺህ ዘመናት የመንግሥት መዋቅር የነበራቸው በእስራኤል ምጽአት መደንገጥ ጀመሩ ። እግዚአብሔር አዳኝነቱ የማይደፈር ግርማ ያላብሳል ።
መዳን በሌላ በማንም የለም ሲባል መዳን በሰዎች ፍልስፍና ፣ ብልሃትና መንገድ አይደለም ማለትም ነው ። /የሐዋ. 4፡12/። መዳን መንግሥትህ ትምጣ ብለን በምንለምነው በክርስቶስ ነው ። መዳን በሌላ በማንም የለም የሚለው ቃል እግዚአብሔርን ላከበሩና ለሚጸልዩልን ቅዱሳን መቃወሚያ ተደርጎ የሚጠቀስ ሳይሆን ክርስቶስን ገድለው ስሙ ሲነሣ ለሚከፉ ሰቃልያነ እግዚእ የተጠቀሰ ነው ። እነዚህ ወገኖች ሌላ አዳኝ የለምና የሰቀሉትን ጌታና አዳኝ ብለው ማመን ነበረባቸው ። መራራ ቢሆንም ለመዳን ይህን ዋጋ መክፈል ነበረባቸው ። ካለንበት ነገር የሚያድነን መድኃኒታችን እግዚአብሔር ነው ። መድኃኒት ለእኛ ሕይወት ሲሆን ለበሽታ ግን ሞቱ ነው ። እግዚአብሔርም ለሚያምኑት የሕይወት ሽታ ፣ ለሚጠፉት የሞት ሽታ ነው ። 2ቆሮ. 2፡14-16 ።
ካለውና ከሚመጣው ክፉ የምታድነን ፣ ከራሳችንም ስህተት የምትጠብቀን መድኃኒታችን አንተ ነህ ።
ክብሩ ይጋርደን !
1ኛ ጢሞቴዎስ /2/
ጥቅምት 26 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም