የትምህርቱ ርዕስ | ተስፋችን ማን ነው ?

“መድኃኒታችን እግዚአብሔር ተስፋችንም ኢየሱስ ክርስቶስ”
                                                 1ጢሞ. 1፡1/
         ሐዋርያው ጳውሎስ በኢየሩሳሌም በ50 ዓ.ም ከተደረገው የመጀመሪያው የሐዋርያት ጉባዔ በኋላ ደግሞም በሁለተኛው ሐዋርያዊ ጉዞው ወጣቱን ጢሞቴዎስን አግኝቶ አስከተለው ። ጢሞቴዎስ ወደ ክርስትና የመጣው በ50 ዓ.ም. ሲሆን ሐዋርያው ጳውሎስ ይህንን የመጀመሪያይቱን የጢሞቴዎስን መልእክት የጻፈለትም በ63 ዓ.ም. ገደማ ነው ። በዚህ ጊዜ ጢሞቴዎስ በክርስትናና በአገልግሎት 13 ዓመታት ያህል ያሳለፈ ነው ። 13 ዓመት የሆነውም አማኝና አገልጋይ ምክር ያስፈልገዋል ። የኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ከተመሠረተች ቢያንስ 8 ዓመት ይሆናታል ። ጢሞቴዎስ የዚህች ቤተ ክርስቲያን ጳጳስ ሁኖ ነበር ። ሐዋርያው ጳውሎስ ወጣቱን መሪ እንዴት በአገልግሎቱ ውጤታማ እንደሚሆን የሚያሳይ የመጀመሪያውን መልእክቱን ጻፈለት ። ይህ ነገር ዛሬ ያሉት አባቶች ከበታች ላለው አስተዳዳሪ የማጽናኛና የጥበብ መልእክት ቢልኩ ታላቅ ደስታ ይሆን ነበር ። ጢሞቴዎስም በዚህ መልእክት እንደ ተደሰተ እርግጠኞች ነን ።

 ሐዋርያው ጳውሎስ ልጅነት የተጫነውን ማርቆስን ቢያጣም እግዚአብሔር ጢሞቴዎስን አዘጋጀለት /የሐዋ. 15፡36-41፤ 16፡1-3/። በማጣት ውስጥ ማግኘት አለ ። በማጣት ውስጥ ያለውን ማግኘት አስቦ ሥራውን የቀጠለ ሰው ያጣውን ቆይቶ ያገኛል ። ምክንያቱም ሐዋርያው ጳውሎስ በኋላ ለዚሁ ለጢሞቴዎስ እንዲህ ብሎታልና፡- “ማርቆስ ለአገልግሎት ብዙ ይጠቅመኛልና ይዘኸው ከአንተ ጋር አምጣው ።” /2ጢሞ. 4፡11/ ። ስለሄዱት ሳይሆን ስለሚመጡት ማሰብ ደስ ይላል ። ሐዋርያው ጳውሎስ በደቀ መዝሙሩ አዝኖ ቢቀር ኑሮ ጢሞቴዎስን አያተርፍም ነበር ። ጢሞቴዎስ እናቱ አይሁዳዊት ፣ አባቱ ግሪካዊ ነው ። ከልጅነቱ ጀምሮ የብሉይ ኪዳን መጻሕፍትን በማንበብ ያደገ ፣ የክርስቶስንም መገለጥ የሚጠባበቅ ሰው ነበር ። እግዚአብሔር ለተጠሙት እርካታን ያዘጋጃልና ይኸው ጢሞቴዎስ አማኝም ጳጳስም ሆነ ። መካሪ መካሪ ፣ መሪው መሪ አያገኝምና ሐዋርያው ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ ይህን መልእክት ጻፈለት ። ስለ ደከሙ ምእመናን እንጂ ስለ ደከሙ አገልጋዮች የሚያስብ የለምና ሐዋርያው የመጀመሪያውን መልእክት ጻፈለት ። ሳያስተምሩ መውቀስ ነውር ነውና ሐዋርያው ይህ ጦማረ ጽድቅ ሊጽፍለት ተጋ ።

 መልእክቱን የሚጀምረው በሰላምታ ነው ። ቤት ደጃፍ አለው ፣ ደብዳቤም ሰላምታ አለው ። ሰላምታ ልብን የሚያንኳኳ የፍቅር ምት ነው ። ሐዋርያው ሰላምታውን በስሙና በፍቅሩ ሳይሆን በእግዚአብሔር ስምና ፍቅር ይጀምራል ። የሰው ስም የሚሻር ፣ ፍቅሩም የማይቆይ ነውና ። ገና በሰላምታው ተስፋው ማን መሆን እንዳለበት ይነግረዋል ።
 ሐዋርያው ስለ ተስፋ መሠረት ለመናገር ምነው ተጣደፈ ? ከሰላምታው የተስፋው ድምፅ ምነው ቀደመ ? የሚል ካለ በአጉል ተስፋ ልብ እየተነነ እንደሆነ ስለ ተረዳ ነው ። በዚህ ዓለም ላይ የሰውን ጉልበት ከሚጨርሱ ነገሮች አንዱ ያልተፈጸሙ ተስፋዎች ናቸው ። በዚህ ምክንያት ወዳጅ በወዳጁ ጽኑ ቅያሜ ያቄማል ፣ ሕዝብም በመሪዎቹ በብርቱ ያዝናል ። ሰዎች የሰጡትን ተስፋ ለመፈጸም የሚቸገሩት፡-
1-  ታማኝነትን በማጣት ፣
2-  አቅም በማጣትና
3-  ፍላጎት በማጣት ነው ።
ተስፋን መስጠትና መፈጸም ለራስ የሚደረግ ክብር ነው ። እግዚአብሔር ታማኝ ነው የምንለው ተስፋን ስለሚፈጽም ነው ።  አምስቱ ብሔረ ኦሪት የሚባሉት ከዘፍጥረት እስከ ዘዳግም ያሉት መጻሕፍት እግዚአብሔር ተስፋ የሰጠባቸው ሲሆኑ መጽሐፈ ኢያሱ ግን ተስፋው የተፈጸመበት ነው ። ዓመታት ቢረዝሙም እገዚአብሔር የሰጠውን ተስፋ አይዘነጋም ።
ተስፋ ያደረግናቸው ነገሮች ብዙ ናቸው ። ተስፋ የሰጡን ሰዎች ግን የነፋስ ጭራ ሆነው የት እንዳሉም ማወቅ አልቻልንም ። ተስፋቸውን ታምነን የያዝነውን ጥለን የጠበቅናቸው ሕልም ሁነው ቀርተዋል ። ማፈር ደከመኝ እስክንል ተስፋዎቻችን ዱዳ አድርገውናል ። የዓመቱን በዕለት የዘመናቱን በዓመት እንደሚፈጽሙልን ቃል የገቡልን ያለንን ነገር ሲያሳጡን ተክዘናል ።መጽሐፍ ግን ተስፋችን ክርስቶስ መሆኑን ይነግረናል ። ዝለት በጽናት እንዲለወጥ ዛሬ ተስፋችንን ክርስቶስ ልናደርግ ይገባናል ። በመጀመሪያው ምጽአቱ የአዳምን ተስፋ የፈጸመ ነው ። በሁለተኛው ምጽአቱ የቤተ ክርስቲያንን ተስፋ የሚፈጽም ነው ። ተስፋውን ለመፈጸም ከልካይ የለውም ። ምክንያትም ሳያቀርብ ከተፈጥሮ በላይ ይሠራል ። ትዝብትን ሳያስብ ለታማኝነቱ ይተጋል ። ተስፋችን ማን ነው ?
ጥቅምት 24 ቀን 2012 ዓ.ም.
ዲአመ
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም