መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እንዲህ ቢሆንስ » እንዲህ ቢሆንስ …? /3/

የትምህርቱ ርዕስ | እንዲህ ቢሆንስ …? /3/

“ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ እንደሆኑ አምናለሁ ። በዛሬ ዘመን ግን መውለድ ያስፈራኛል ። ልጆቼ ከእኔ ፈቃድ ውጭ ቢወጡስ ብስጭቱን እችለዋለሁ ?” እያልህ ይሆን ? ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ብቻ ሳይሆኑ የእግዚአብሔር አደራም ናቸው ። ልጆችህን ከእውቀትህ ብቻ ሳይሆን ከሕይወትህም ልታስተምራቸው ይገባል ። በተፈጥሮ ካንተ የሚወስዱት ጠባይ እንዳለ ሁሉ በልምምድ ደግሞ ካንተ የሚወርሱት ነገር አለና ከመውለድ በፊት የሕይወት ለውጥ ወሳኝ ነው ። አንተ አልኮል እየጠጣህ መጠጥ ክፉ ነው ብትላቸው አንደኛ ስትስማቸው በትንፋሽ ታስለምዳቸዋለህ ፣ ሁለተኛ እንደ ተከለከሉ እንጂ መጥፎ እንደሆነ አይረዱምና ሲያድጉ የመጀመሪያ ሥራቸው አልኮል መቅመስ ይሆናል ። ልጆች የአዳሪ ተማሪ ናቸውና የሚማሩት ከሕይወትህ ነው ። በዚህ ዓለም ላይ የእነርሱ ንጉሥም ጳጳስም አንተ ነህና አንተን ያያሉ ። ልጆችህ ባንተ ላይ ስላላቸው እምነት እንኳ መለወጥ ግድ ይልሃል ።
ልጆች ላንተ የሚሰጡህ ብዙ ነገሮች አሉ ። ቅዱስ ፍርሃትን ያለማምዱሃል ።እንደ ድሮው ተቆጡኝ ብለህ ቡጢ መሰንዘር ፣ ተናገሩኝ ብለህ ሥራ መልቀቅ አይታሰብም ። ስለ ልጆችህ ስትል ትዕግሥትን ትለማመዳለህ ። እግዚአብሔር ትዕግሥትን የማይወደውን የሰው ማንነት መታገሥን ከሚያለማምድበት መንገድ አንዱ መውለድ ነው ። ስለ ፍቅር ግድ የሌለህና ስለ ፍቅር በሚያወሩ የምትስቅ ከነበርህ እግዚአብሔር በትንሹ ሕፃን ፍቅር አቅልህን/አእምሮህን ይቆጣጠረዋል ። አንተን ትልቁን ሰውዬ በትንሹ ሕፃን ቆዳ ጠቅልሎ ልክህን ያሳይሃል ። እንደሚወድህ ማረጋገጥ ሳትፈልግ የምትወደው ልጅህን ነውና ምክንያት የለሽ ፍቅርን በልጆች ትማራለህ ። ከመውለድ በፊት ያየኸው ልብስ ያምርህ ነበረ ፣ አሁን ግን ለልጄ ትላለህ ። ራስ ወዳድነትን እየጣልህ እንደሆነ እወቅ ። ትልቁ የገነት ኃጢአትና የሞት በር ራስ ወዳድነትን የምትጥለው አንዱ በመውለድ ነው ። የወላጆችህ ፍቅር ብዙም ግድ አይሰጥህም ነበረ ፣ እንደ ጤንነትም አትቆጥረውም ነበረ ፤ “ወልደህ እየው” ሲሉህም ምርቃት መስሎህ ነበረ ። አሁን ግን ወላጆችህ ላንተ የከፈሉት ዋጋ ይገባሃል ። መውለድ በወላጆችህ ላይ የነበረህን ግድ የለሽነት ያስጥልሃል ። መቼም ሁሉም ወላድ በዚህ መንገድ ይማራል ማለት አይደለም። እግዚአብሔር ቀና ሰዎችን ሁሉን ለትምህርት ያደርግላቸዋል ማለት ነው ።
ልጆች ዋጋ እየከፈልህ የምትወዳቸው ናቸው ። እነርሱ ከመጡ በኋላ የቤት ወጪህ ጨምሯል ። የኖረው ብርጭቆ ይሰባበራል ። ነገር ግን ከሚያከስሩህ የሚሰጡህ ደስታ ይበልጣልና ደግመህ አታስበውም ። የመጀመሪያ ልጅህን ስትወልድ አዲስ ስለሆንህ አንተም ተጨንቀህ ልጁንም ታስጨንቃለህ ። ልጁን ብቻ ሳይሆን ነጻነቱንም ትወደዋለህ ። ልጄ ይህን መምሰል አለበት ብለህ የሳልከውን ሥዕል ከመጀመሪያ ልጅህ ትጠብቃለህና ዱላና ቁጣ ታበዛበታለህ። ገና እስከ ሰማንያ ዓመት የሚማረውን በሰማንያ ወራት እንዲማርልህ ትፈልጋለህ ። ስለዚህ የመጀመሪያ ልጅህ ሳታውቀው ትጎዳዋለህ ። ኋላ ላይም ትንንሾቹ አጥፍተው እርሱን ትገርፋለህ ። በሁለተኛው ልጅ ትንሽ ትበርዳለህ። ሦስተኛው ላይ ከፍቅር በላይ ስለ ምቾቱ ታስባለህ ። በአራተኛው ላይ ልጁን ወደህ ነጻነቱን ትተውለታለህ ። ብዙ ጊዜ የመጨረሻ ልጆች የማይነኩት ለዚህ ነው ። አንተም ይደክምሃል ፣ ሁሉም ነገር በጊዜው እንደሚሆን ታምናለህ ። የመጀመሪያ ልጅህ የጉብዝና በትርህ ስላረፈበት ገሸሽ ሲልህና ሲወቅስህ ፣ የመጨረሻው ግን ድካምህንና ፍቅርህን ብቻ ስለሚያውቅ ያዝንልሃል ። ሁሉም ልጆችህ የመጨረሻው ላይ ጥለው አንተን ይረሱሃል ። ብቻ መውለድ መልካም ነው ፣ የመውለድ መጨረሻው ግን መሐንነት ነው ። ሁሉም የራሱን ኑሮ ሲጀምር ቤትህ ፀጥ ይላል ። በድሀ አገር ልጆች የሚወለዱበት ምክንያት ይጦረኛል በማለት ነው ። የሚጦር ግን እግዚአብሔር ነው ።
እምነትህን በእግዚአብሔር ላይ አድርግ እንጂ ወርደህ በልጅ አትታመን ። ዳዊት ለልጆቹ በጣም ይሳሳ ነበር ። አምኖንን በጥፋቱ ትቶታል ፣ አቤሴሎም ወንድሙን ገድሎም መልሶ ባብቷል ። ነገር ግን የሳሱለት ዘመድ አይሆንምና ልጆቹን ከስሯል ። ደግ ነኝና ደግ ልጅ እወልዳለሁ ብለህ አታስብ ። እንዳንተ የሆንከው አንተ ብቻ ነህ ። ልጅህ ከባሕርይህ የተከፈለ እንጂ ተቀጥሎ የሚኖር አይደለም ። የራሱ ምርጫ አለው ። ደጉ ዳዊት ዓመፀኛ እንደ ወለደ አትርሳ ። የዓመፀኞቹ የአዳምና የሔዋን ልጅም አቤል መሆኑን አስታውስ ። ዓለም ለግምት አይሆንም ። ካህኑ ዔሊ ልጆቹን ለመቆጣት እንኳ ሳሳ ። በመጨረሻ ልጆቹንም አጣ ። እርሱም አጉል ሞት ሞተ ። አዎ ልጅህን ገሥጽ ፣ አስተምር ። ልጅህን በዱላ ስትቀጣ ግን በጣም ተጠንቀቅ ።ሰይጣን እያንዳንዱን ገጠመኝ የሞት ምክንያት እንዲሆን ይሠራልና በጣም አስብበት ። በጥፊ የሞቱ ፣ በአንድ አለንጋ እዚያው የቀሩ አሉ ።
ደግሞም በዚህ ዘመን እንዴት እወልዳለሁ አትበል ። በየትኛውም ዘመን ኃጢአት ነበረ ። ልጅ የእግዚአብሔር ሲሆን ላንተ ግን ስጦታ ነው ። በልጅ ምክንያት እምነት እንዳታጣ ተጠንቀቅ ።
አንድ ትልቅ ባለሥልጣን የነበሩ ሰው እንዲህ ብለው መከሩኝ ፡- “አሥራ ሁለት ልጅ ወልጃለሁ ፣ አንዱም አይመስለኝም ፣ ሁለት መጽሐፍ ጽፌአለሁ የእኔን አሳብ ያንጸባርቃሉ ። ልጅ እንደ ራሱ ነው ፣ መጽሐፍ ግን እንዳንተ ነው ። ስለዚህ ጻፍ “ ብለውኛል ። አዎ ልጅ የራሱን አሳብ ቢከተል ብዙም አትጨነቅ ። ወጉ ነው ። አንተ ግን የቀናውን መንገድ ምራው ። በጠዋት የመከርከው በማታም ይሰማሃል ። በልጅነቱ ያነጽከው በጎልምስናውም ያከብርሃል ። ላንተ ፍቅር እንዲኖረው እርሱን በጣም አትውደድ ፣ እናቱን ስትወድ ፣ ያን ጊዜ ላንተ ፍቅር ይኖረዋል ። ላንቺ ያለውን ፍቅር ልጅሽ የሚረዳው አባቱን ስትወጂ ነው ። ብዙ ባለ ትዳሮች ያልተረዱት ምሥጢር ይህን ነው ። ሲወልዱ የትዳር ፍቅራቸውን ሁሉ ለልጁ ይሰጣሉ ። በረከቱን ሕይወት አድርገው ይኖራሉ ። ቢሆንም መውለድ ስጦታ ነውና አለመውለድም ስጦታ ነው ። ሁሉ አይወልድም ፣ መውለድም አንድ ዓይነት ብቻ አይደለም ። የተወለዱትን መታደግም መውለድ ነው ። ያልወለዳችሁም አመስግኑ ። እግዚአብሔር ያየውን አይቶ ይከለክላልና ። የማትወልዱት መንፈስ እየተዋጋችሁ ነው ከሚሉና ነጻ እናውጣችሁ ከሚሉ ተጠንቀቁ ። ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታ ናቸው ከተባለ እግዚአብሔር ልኮ ማን ያስቀረዋል ?
ወደ ክርስቶስ መገስገስ 8
ተጻፈ በአዲስ አበባ
መስከረም 27 ቀን 2011 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም