መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ባለህ ተደሰት

የትምህርቱ ርዕስ | ባለህ ተደሰት

October 3, 2021 by ዲያቆን አሸናፊ መኮንን

ባለህ ተደሰት

“የምንወደውን ማግኘት ካልቻልን ፣ የምናገኘውን እንውደድ ።” /ስፓኒሾች/

በዚህ ዓለም ላይ ትልቁ ፍልስፍና ፣ ትልቁ ጥበብ ፣ ትልቁ እምነት “እንደ ፈቃድህ” ማለት ነው ። በእግዚአብሔር ፈቃድ ወደዚህ ዓለም መጥተናል ፣ በእግዚአብሔር ፈቃድ ከዚህ ዓለም እንሄዳለን ። የእግዚአብሔር ፈቃድ ገዥ ነው ። ፈቃድህ ይሁን ባንልም ፈቃዱ ይሆናል ። ፈቃዱ ይሁን በማለት ግን ሕይወት ጥያቄ ሳይሆን መልስ እንድትሆን ያደርጋል ። ትልቅ ፍልስፍና ራስን መጣል አይደለም ፣ ራስን መጣል ስንፍና ነው ። ፈላስፎች ከምድር ጀምረው በምድር ይጨርሳሉ ። ያለ ክርስቶስም ለዚህ ዓለም ስለሚሞቱ ትንሣኤ የላቸውም ። ዓለም ከንቱ ናት ቢሉም ብርቱ በሆነው በክርስቶስ ግን አልቀየሩአትም ። ትልቅ ፍልስፍና የሕይወቴን መግቢያና መውጫ ለያዘው እግዚአብሔር መንገድ መልቀቅ ነው ። ያለ ፈቃዴ መጥቼ ያለ ፈቃዴ በምሞትበት ዓለም ላይ ፈቃድህ ይሁን ማለት ምቹ ትራስ እንጂ የድንጋይ መደገፊያ አይደለም ። ትልቅ ጥበብም የእግዚአብሔርን ፈቃድ ማወቅና ማክበር ነው ። ጥበብ እውቀትን የምንኖርበት ተግባራዊነት ፣ እሾሁን ሳይሆን ጽጌረዳውን የምናይበት መነጽር ነው ። “የማይጋፉትን ግንብ ዞረው ያልፉታል” እንዲሉ የማንጋፋውን ፈቃድ መቀበል ከመጋጨት ያድናል ። ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ሲጣላ ቀጥሎ ከሰው ጋር ሳይሆን ከራሱ ጋር ይጋጫል ። ከራሱ ጋር የተጋጨም ከሰው ጋር ሰላም የለውም ። ትልቁ እምነትም ተአምራት ማድረግ ሳይሆን “ፈቃድህ ይሁን” ብሎ ማረፍ ነው ። ያለ እግዚአብሔር ፈቃድ የተሰጠን ነገር እንደሌለ ያለ ፈቃዱም የሚወሰድብን ነገር የለም ።

ይህች ዓለም ጉድለትዋ የጀመረው ዛሬ ሳይሆን አዳም በስደት ከመጣባት ጊዜ አንሥቶ ነው ። ለምለም እንድታበቅል የተፈጠረችው እሾህ አሜኬላ ሲበቅልባት ፣ እየደሙና እያደሙ መኖር ሲበዛባት ፣ አንዱ ላንዱ ዕረፍት መሆን ትቶ ሐፍረት ሲሆንባት ዓለም ከንቱ ነው እንላለን ። ዛሬ የጀመረ የመሰለን ክስተትም ኃጢአትም የለም ። የሚሆነው ሲሆን የነበረ ነው ። “ደንቆሮ የሰማ ቀን ያብዳል” እንዲሉ አላዋቂ ዛሬ ሲሰማ ያ ነገር ዛሬ የጀመረ ይመስለዋል ። ልቅሶ ላልሰማው ሰው ሁልጊዜ አዲስ ነው ። ሰውዬው ሚስቱ በሞተች ባመቱ የሰማ ሰው መጥቶ ሲያለቅስ “እኔ ረስቻታለሁ አንተ እስካሁን ታስባታለህ” አለ ይባላል ። ፍላጎታችንን በውል መረዳት በማንችልበት ዓለም ላይ ነን ። ትላንት የምንፈልገውና ዛሬ የምንፈልገው እርስ በርሱ የሚቃረን ነው ። በምኞት ስንሰጥ ኖረን ስናገኝ ስስታም ነን ። ሁሉም ነገር ቢሟላ ዓለም ዓለም መሆንዋ ይቀር ነበር ። “ብልህ ልጅ የሰጡትን ይዞ ያለቅሳል” እንዲሉ የመጣውን መቀበል ያልመጣውን ለመጠበቅ ኃይል ነው ።

ብዙ ሰው ከፍላጎቱ ውጭ የተማረ ፣ የሚሠራ ፣ የሚኖር ሊሆን ይችላል ። የሚወደውን ነገር ያገኘ ጥቂት ነው ። ዕለት ዕለት የምንሸከመው መስቀል የማንወደውን ነገር መታገሥ ነው ። ደስታን ማሳደድ በበዛበት በዛሬው ዘመን ፣ ደስታ ላግኝ እንጂ በየትም በኩል ይምጣ በሚባልበት በእኛ ዓለም ፣ በቆሻሻ ውኃም ቢሆን እሳትን ማጥፋት ይቻላል ተብሎ ከእውነት ስሜት በሚከበርበት ምድር የሚወዱትን ማጣት ብርቱ ነገር ነው ። በዚህ ምድር ላይ የምንኖረው ግን የምንወደውን ስላገኘን ብቻ ሳይሆን በማንወደው ነገር ውስጥም ትዕግሥትን ለመለማመድ ነው ። እንደ እኛ አሳብ በዚህ አገር ፣ በዚህ ኑሮ ውስጥ አልነበርንም ። ከመረጥነው የተመረጠልን ይሻላልና ደስ ሊለን ይገባል ። የትም ቢሄዱ ሰማይና አፈር አንድ ነው ። የትም ቢሄዱ ምግብ የሚባል ነገር አናገኘም ፣ የምግብ ልዋጭ እንጂ ። እግዚአብሔር ብቻ እንግዳ ደስታ ነው ።

የምንወደው ወዳጃችን ፣ የመከራችን ጓድ ዛሬ በቅርበትም በሕይወትም ላይኖር ይችላል ። ከሩቅ ዘመድ የቅርብ ጎረቤት ይሻላልና ያገኘነውን መውደድ ያስፈልጋል ። ሰው የሚኖረው ወዳጁ ያለበት ሳይሆን እንጀራው ያለበት ነው ። እየተዋደድን ከብዙ ወዳጆቻችን ጋር በእንጀራና በሞት ምክንያት ተለያይተናል ። ዛሬ ያሉት ወዳጆቻችን እንደ ቀድሞዎቹ ላይሆኑልን ይችላሉ ። ፍቅር እየቀነሰ ባለበት ዘመን ባለመጥፋቱ ማመስገን ይገባናል ። ከመልካምና ከክፉ ማነጻጸር በድሎት ዘመን ነው ። በክፉ ዘመን ከክፉ የተሻለው ክፉ ይመረጣል ።

የምንወደውን ትምህርት እየተማርን ላይሆን ይችላል ። ሰው ግን የሚኖረው በትምህርቱ ሳይሆን እግዚአብሔር በሚሰጠው ዕድል ነውና መከፋትና ማዘን አይገባም ። የትምህርት አንካሳ የለውምና ሁሉን መማር መልካም ነው ። በምንወደው ሥራ ላይ ላንሆን እንችላለን ፣ የምንወደው ጋ ለመድረስ ያገኘነውን መውደድ መሰላል ነው ።

የምንወደውን ማግኘት አለመቻላችን የሚያናድድ ሳይሆን ሰው መሆናችንን የሚያስረግጥ ነው ። ሰው ማለት አቅሙ የተወሰነ ፍጡር ነውና ። እኛ የምንወደው ባይገኝም እግዚአብሔር ይሁን ያለው ግን አልቀረም ። በገጠመን ዕድል ሳይሆን በመረጥነው ክፉ እንጠየቃለን ። እነዚያ ነገሮች ባይሆኑ መልካም ነበር ። ፈቃዳችን ሳይሆን በሆኑት ነገሮች ግን ጸጸት ሊሰማን አይገባም ። ከንቱ ጸጸት ተመጻቂነት ነውና ።

የዛሬ አለመቻል የነገ መቻል ነው ። አለመቻልን እንደ መቻል ስንቀበለው የምንችልበት ቀን ይመጣል ። ትንሣኤ ያለው ትንሣኤ ውስጥ ሳይሆን ውድቀት ውስጥ ነው ። በጠለቀችው ፀሐይ ሳይሆን በወጡት ጨረቃና በፈኩት ከዋክብት አመስግን ። ጨለማ ባይመጣ ከዋክብት አይታዩም ነበር ፣ ክፉ ቀኖችም ሰዎችን ያሳውቁሃል ።

በእጃችን ያለው ትንሽ ነገር ፣ የማንወደው ቢሆንም ደስ ይበለን ። የምንወደው እየቀረበ ይመጣል ። ምስጋና ጨለማን ብርሃን ፣ መንፈሳዊ ደስታም ጉብኝትን ያመጣል ። ባንወደውም ወደ ሞት የምንጓዝ ነንና የምወደው ቀረብኝ ብለን መከፋት አይገባንም ። የምንወደውን ብናገኝም ሞት አይቀርም ። በሥላሴ ማመን ግን ከሲኦል ሞት ያድናል ። የምትወዱትን ስላላገኛችሁ እንኳን ደስ አላችሁ ።

የብርሃን ጠብታ 11

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 23 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም