መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ሁላችንም

የትምህርቱ ርዕስ | ሁላችንም

September 29, 2021 by ዲያቆን አሸናፊ መኮንን

ሁላችንም

“ሁላችን የእግዚአብሔርን ልጅ በማመንና በማወቅ ወደሚገኝ አንድነት ፥ ሙሉ ሰውም ወደ መሆን ፥ የክርስቶስም ሙላቱ ወደሚሆን ወደ ሙላቱ ልክ እስክንደርስ ድረስ ፥ ቅዱሳን አገልግሎትን ለመሥራትና ለክርስቶስ አካል ሕንጻ ፍጹማን ይሆኑ ዘንድ ።” ኤፌ. 4 ፡ 12-13 ።

ጳጳሱ እንዲህ እያደረጉ ካልን ጳጳስ መሆን ያለበትን እናውቃለንና እውቀታችን ከጳጳሱ በላይ ነው ። ጳጳሱ እንዲህ እያደረጉ የምንለው ራሳችንን ነጻ ለማውጣት ነው ። ጳጳስ ምን ማድረግ እንዳለበት እናውቃለንና የምንጠየቀው ከጳጳሱ በላይ ነው ። ቅድስናን ከፋፍለን ይህን መነኩሴ ፣ ይህን ምእመን ሊያደርገው ይገባል እንላለን ። ቅድስና ግን ለምእመናን ሁሉ የተሰጠ እንጂ ለጥቂቶች የተጣለ ግዴታ አይደለም ። እግዚአብሔር ቅድስናን ሲሰጠን ተጨንቀን እንድንፈጽመው ሳይሆን ለምድራዊ ደስታችንም አስቦ ነው ። ሐሰተኛ ደስታ በምድር ላይ አለ ፣ እውነተኛውን ደስታ የምናገኘው ግን በቅድስና ነው ። በድሎ ያረፈ ፣ ተቀድሶ የተጨነቀ የለም ። ወንጌላውያን ሰባኪ ሊሆኑ ይችላሉ ፣ ምእመናን ሁሉ ግን እንደ መግደላዊት ማርያም የትንሣኤው ምስክር ናቸው ። ክርስቶስ ተነሣ ብቻ ሳይሆን በክርስቶስ ተነሣሁ ብለው መመስከር የምእመናን ግዳጅ ነው ። ወደ መንሥተ ሰማያት የምንገባው በአማኝነት እንጂ በካህንነት አይደለምና ለምእመንነት ዋጋ መስጠት ይገባናል ። የክህነትም መነሻው አማኝነት ነው ። የመንግሥት ባለሥልጣናት አገር እየዘረፉ እንላለን ፣ እኛ ግን የአገራችንን ሀብትና ጊዜ ጭምር መስረቃችንን እንደ ቀላል እናየዋለን ። በየመሥሪያ ቤቱ ሰውን የሚያስለቅሱ ሠራተኞች አብዛኛዎቹ ሃይማኖት አለን ብለው የሚናገሩ ናቸው ። ሃይማኖት የሌላቸው ሕዝቦች ስለሚከፈላቸው በትጋት እየሠሩ እኛ ግን በሃይማኖትም በደመወዝም ሁነን ሰው እናሰቃያለን ።

እርስዋ ቤቱን ጥላ እየዞረች ነው የሚለው ምሽት ስድስት ሰዓት የሚገባው ባል ነው ። ካህኑ ይህን ግፍ እያዩ ለምን አያወግዙም እንላለን ፣ ግፍን ለማውገዝ ሁሉም ካህን መሆኑን አናስተውልም ። የመጣውን ዕዳና የሚመጣውን መከራ ለጥቂት ሰዎች ማሸከም እንፈልጋለን ። ለምትናወጥ መርከብ ጥፋቱ የካፒቴኑ ነው የሠራተኞቹ ብንል ማዕበሉ ጸጥ አይልም ። ሰበብና እገሌ ነው እያሉ መጠቆም የመጨረሻው ዘመን ምልክት ነው ። ማቴ. 24፡10 ።

ሐዋርያው ግን “ሁላችን” በማለት ይናገራል ። ሁላችን የሚጠበቅብን ነገር አለ ። ማመን ፣ ማወቅ ፣ አንድነት ፣ ሙሉ ሰውነት ፣ እስከታቀደልን ድረስ ማደግ ፣ የተቀደሰ አገልግሎት ፣ የጠፉትን የክርስቶስ አካል ማድረግ ከሁላችን ይጠበቃል ። ትንሽ ለመዘርዘር እንሞክር ። ሁላችን ማመን ይገባናል ። እግዚአብሔር ፀሐይን ለሁሉ እንደ ሰጠ ፣ የሰው ልጆችም ሁሉ የፀሐይን ጌታ ማመን ይገባቸዋል ። ስጦታውን ወዶ ሰጪውን ጠልቶ የትም መድረስ አይቻልም ። እውቀትና ፍልስፍና የማይመልሳቸው የሕይወት ጉዳዮች አሉ ። ማን ፈጠረኝ ? ለምን እኖራለሁ ? ወዴት እሄዳለሁ ? የሚሉት የሕይወት ጥያቄዎች በእምነት ብቻ መልስ ያገኛሉ ። እምነት ከእኔ የበረታ ኃይል አለ ብሎ “ደካማው ብርቱ ነኝ” በማለት የሚፎክርበት ምሥጢር ነው ። ኢዩ. 3 ፡ 10 ፤ ሚክ. 7 ፡ 8 ። እምነት ከተፈጥሮ በላይ የሆኑ ተአምራቶች የሚደረጉበት ብርሃናዊ ዘንግ ነው ። እምነት የማይቻለው የሚቻልበት ነው ። እያንዳንዱ ኑሮአችን ከእምነት ጋር የተያያዘ ነው ። ባናምን ኖሮ አንተኛም ነበር ። ባናምን ኖሮ ከቤት አንወጣም ነበር ። ባናምን ኖሮ የቅድሙን ምግብ አንበላውም ነበር ። እምነት ለምድርም ለሰማይም አስፈላጊ ነው ። ማመን የሚገባን ሁላችንም ነን ።

ማወቅ ሁላችንም ይገባናል ። እያወቅን እናምናለን ፣ እያመንን እናውቃለን ። እግዚአብሔርን ጠንቅቆ ያወቀው ሰውም መልአክም የለም ። ማወቅ ያሳስተናል የሚሉ ሰዎች አሉ ። መጽሐፉ ደግሞ “ሕዝቤ እውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቷል” ይላል ። ሆሴ. 4፡6 ። እያንዳንዱ ክርስቲያን የነገረ መለኮት ተማሪ ነው ። ቅዳሴው ፣ ስብከቱ ሁሉ ነገረ መለኮት ነው ። ሁላችን አንድነት ያስፈልገናል ። የአንድነት ነገር “ቁጭ ብለው የሰቀሉትን ቁመው ማውረድ ይቸግራል” ዓይነት ሁኖብናል ። ግንብን መገንባት መለያየትን መፍጠር እውቀት አይጠይቅም ፣ ድልድይ መዘርጋት አንድነትን መፍጠር ግን ብስለት ይጠይቃል ። አንድ ፀሐይ እየሞቅን መለያየታችን ይገርማል ። ከእንስሳት ጋር እንኳ በሥጋ ዘመድ ነን ። ከመላእክት ጋርም በነፍስ ዘመድ ነን ። እኛን ከሚመስል ሰው ጋር ደግሞ የበለጠ ዘመድ ነን ።

ሙሉ ሰውነት ይጠበቅብናል ። ሙሉ ሰው ራሱንና ያዳነውን በትክክል የሚያውቅ ነው ። ላመነበት ነገር መልስ መስጠት የሚችል ነው ። አዩኝ አላዩኝ እያለ የሚኖር ሳይሆን ለቃል ኪዳኑ ታማኝ የሆነ ነው ። ይህን ካወቅሁ ይህን ካደረግሁ በቃኝ ማለት ሳይሆን እስከታቀደልን ድረስ ማደግ ከሁላችን ይጠበቃል ። የዓለም ታሪክ የጥቂት ሰዎች ታሪክ ነው የሚባለው ጥቂቶች ሠርተው ወይም ጎልተው ስለሚወጡ ነው ። ለሥራ እንጂ ለተመልካችነት የተፈጠረ የለም ።

ሁላችንም የተቀደሰ አገልግሎት ይጠበቅብናል ። ብራብ አብልታችሁኛል የሚለው የተቀደሰ አገልግሎት ነው ። ታመው በቤት የቀሩ ፣ ረሀብ በሽታ ሆኖ የሚያሰቃያቸው ፣ ልብስ በማጣት አፍረው ከቤት የማይወጡ ፣ በግፍ ታስረው በወኅኒ ያሉ ብዙ ወገኖች አሉ ። ይህን የተቀደሰ ተግባር ለእርዳታ ተቋማት መስጠት ተገቢ አይደለም ። በጎ ነገር ለሰው ልጅ እንጂ ለድርጅት አልተሰጠም ። ከአካሉ ርቀው የሚኖሩትን በሚመለከት እገሌ ሰባኪ ባገኛቸው ማለት ሳይሆን ሁላችንም ወደ መንፈሳዊው ኅብረት ልናቀርባቸው ይገባል ። ሁላችንም የሚለውን እናስተውል ። እገሌ ይሥራው ፣ እገሌ ነው ጥፋተኛው ማለት የትም አያደርሰንም ። ሁላችን ብንነሣ በዓለም ላይ ያለው ጉድለት ሞልቶ ያድር ነበር ።

ጌታ ሆይ አግዘን ። ሥራችንን ሌሎች ሲሠሩልን የሚያፍር ልብ ስጠን ።

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

መስከረም 19 ቀን 2014 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም