የትምህርቱ ርዕስ | የአርምሞ ትሩፋቶች

4   ቅርታ
የአርምሞ ሕይወት ይቅርታን ለመለማመድ ምቹ መንገድ ይሰጣል ። ብዙ ጊዜ ስናገር ይቀለኛል ብለን እናስባለን ። ስንናገር ግን የበለጠ እየተቀጣጠልን ውስጣችን በቂም እያመረቀዘ ይመጣል ። የምንናገርበት መንገድ ክርስቲያናዊ ከሆነ ፈውስ አለው ። በሁለት ዓይነት መንገድ ንግግሮች ይኖራሉ ። የመጀመሪያው በወቀሳ መንገድ ሲሆን ሁለተኛው ግን በክስ መንገድ ነው ። ወቀሳና ክስ ፍጹም የተለያዩ ነገሮች ናቸው ። የወንድማችንን አንድ ዓይነት በደል በመንፈስ ቅዱስ ዓይን ማየትና በሰይጣን ዓይን ማየት ነው ። ወቀሳ የመንፈስ ቅዱስ ነው ፥ ክስ ደግሞ የሰይጣን ነው። ወቀሳ ለሰውዬው ሲሆን ክስ ግን ለሌሎች ነው ። ወቀሳ በር ዘግቶ የሚደረግ ሲሆን ክስ ግን በአደባባይ ነው ። በወቀሳ መንገድ መነጋገር የተቋረጠውን ግንኙነት ይመልሳል ። ክስ ግን ተናጋሪውንም ተከሳሹንም ሰሚውንም ይጎዳል። ያሰብነውን እንናገራለን የሚለው ሁሉም ሰው የሚቀበለው የተለመደው መርሕ ነው ። የተናገርነውን እንደምናስብ ግን ብዙ ጊዜ አንረዳም ። በንዴት ሰዓት በክርክር ጊዜ በድንገት ከአንደበታችን የሚወጡ ከዚህ በፊት አስበናቸው የማናውቃቸው ንግግሮች አሉ ። አንድ ጊዜ ከአንደበታችን ስለወጡ እንደገና እናስባቸዋለን ። ለተናገርናቸው ነገሮች ታማኝ ለመሆን እንሞክራለን ። የተናገርነውን ማሰብ ማለት ይህ ነው ። አርምሞ ከዚህ ስህተት ይጠብቀናል ። ሌሎች በእኛ ላይ ያደረሱትን በደል የምንናገር ከሆነ እያደስነው እንመጣለን ። ከዚህ ሊገላግለን የሚችለው ነገር ምንድነው ? ስንል ፡-

1-  የሆነብን ሲሆን የነበረ እንጂ አዲስ አለመሆኑን ማሰብ
2-  የነገሮችን አስቂኝ ጎናቸውን ፈልጎ ተጨማሪ ደስታ ማድረግ ። አንድ ፈላስፋም ፡- “ኀዘንና መከራን የቀልድ መንገድ ማድረግ ያስፈልጋል። ካልሆነ ማበድ ይከተላልና” ብሏል ። ይኸው ሰው ፡- “የሕይወትን ግብ ማወቅ ፈተናን ለመቋቋም ብቻ ሳይሆን ከሚያዋዥቅ አቋምም ያድናል ። አሸናፊም ያደርጋል” ብሏል ።
3-  ክርስቶስ እንኳ በዚህ ምድር ላይ ብዙ መከራ ተቀብሏል ። ለትልቁና ለቅዱሱ ጌታ ያልተመለሰ ዓለም ለእኔ አይመለስም ብሎ ማሰብ ልበ ሰፊነትን ያጎናጽፋል ።
4-  በዝምታ ፥ መጽናናት በሞላበት አርምሞ ይቅርታን መለማመድ ይገባል ።
 ጻድቁ ኢዮብ ከመከራው በላይ መከራውን የሚተነትኑ ባልንጀሮቹ በብርቱ አቊስለውት ፥ በቊስል ላይ ጥዝጣዜ ሆነውበት ነበር ። የመከራው ማዕበል ካለፈ በኋላ እግዚአብሔር የኢዮብን ባንጀሮች ገሰጻቸው ። ኢዮብም እንዲጸልይላቸው ነገራቸው ። “ኢዮብም ስለ ወዳጆቹ በጸለየ ጊዜ እግዚአብሔርም ምርኮውን መለሰለት እግዚአብሔርም ቀድሞ በነበረው ፋንታ ሁለት እጥፍ አድርጎ ለኢዮብ ሰጠው”  /ኢዮብ .42፥10/ ። እግዚአብሔር ሁለቱንም ወገኖች ሲወቅስ እናያለን ። ኢዮብ አዝኖባችኋል ፥ የጸሎታችሁ መንገድ ተዘግቷል አላቸው ። ኢዮብም በመቀየሙ በረከቱ ተይዞበት ነበር ። የኢዮብ ወዳጆች መጥተው አብረውት መሥዋዕት ባሳረጉ ጊዜ ሁለቱም ተፈቱ። መሥዋዕታቸው ሰመረ ። የኢዮብም ምርኮ ተለቀቀ ። በይቅርታ ውስጥ አእምሮ ሰላም ፥ ልብ ደስታ ያገኛል ። ለመራመድ ጉልበት ፥ ለመጸለይም አቅም ይኖራል ። አህያ ጅብን ከያዘችው በጥርሷ ትገድለዋች ። ነገር ግን በፍርሃት ስለማትለቀው ተመርዛ ትሞታለች ። ሌሎችም በቂም ነክሶ መያዝ ሙት እንደ መንከስ ሁኖ ይገድላል ።
 ይቅርታን ከሚያዘገዩ ነገሮች አንዱ አንደበት ነው ። እግዚአብሔርን መፍራትና መጠበቅ ያለበት አርምሞ ግን ለይቅርታ ያሰናዳል ። የአርምሞ ሕይወት የነበራት እመቤታችን ድንግል ማርያምም የይቅርታ ሕይወት ነበራት። ልጅዋን በመስቀል ላይ በግፍ ሲሰቅሉት አልተቀየመችም ። ታላቅ ኀዘን ብታዝንም ውስጧ ግን በቀል አልነበረም ። ጌታችን የተሰቀለበት አንዱ ምክንያት ራሱን የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ይላል የሚል ክስ ነበር ። እርስዋ ግን ገና ከጽንሰቱ የእግዚአብሔር ልጅ መሆኑን ታውቅ ነበር ። በዚህች ሐሰተኛ ዓለም ግን አልተደነቀችም ። መልስ ለመስጠትም አልሞከረችም ። ልጇ ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር አስተካከለ ብለው ሲገድሉት ሰብአ ሰገል ያቀረቡለትን ስግደትና እጅ መንሻ ብታውቅም አሁንም ቅር አልተሰኘችም ። ውስጧ ይቅርታ ያደርግ ነበር ።
 “እነዚህ ሁሉ ከሴቶችና ከኢየሱስ እናት ከማርያም ከወንድሞቹም ጋር በአንድ ልብ ሆነው ለጸሎት ይተጉ ነበር” ይላል /የሐዋ. 1፥14/ ። ይህ ጊዜ ጌታችን ካረገ በኋላ በመካከል ባለው አሥር ቀናት ውስጥ ነው ። እመቤታችን በጸሎት የምትተጋው “አላውቀውም” ብሎ ከካደው ከጴጥሮስ ጋር ትንሣኤውን ለማመን ከዘገየው ከቶማስ ጋር ነበር ። ስም ዝርዝራቸው ተጠቅሶአል /የሐዋ. 1፥13/። እናቶች ምንም የፍቅር ልብ ቢኖራቸውም ልጃቸውን የነካባቸውን መቀየም እንደ ትክክለኛነት ይመለከቱታል ። ልጃቸው ይቅር ቢል እንኳ እነርሱ ይቅር ለማለት ፈቃደኛ የማይሆኑበት ጊዜ ይበዛል ። እመቤታችን ግን እናት ብቻ ሳትሆን አማኒም ናትና የይቅርታ ልብ ነበራት ። ከነጴጥሮስና ከነ ቶማስ ጋር በጸሎት የሚያተጋ ይቅርታ ብቻ ነው ። ጊዜው የራቀ ነው እንዳንል አርባ ቀን ያህል የሚሆነው ነው ። መንፈሳውያን ሰዎች የይቅርታን ሕይወት አስቀድመው ስለሚይዙ በጉዳት ቀን ይቅር ለማለት አይታገሉም ። የይቅርታ ትግል እንዳይመጣ ፡-
1-  ሰዎችን እንደ ራሳችን መውደድ መልካም ነው ። ራሳችን ለቊጥር በሚያታክት መልኩ ያጠፋል ። ዘወትር አብረነው የምንኖረው ይቅር ስለምንለው ነው ። የይቅርታችን ምክንያቱም ራሳችንን ከጥፋታችን ለይተን ማየታችን ነው ። ሰዎችንም እንደ ራሳችን ስንወዳቸው ከጥፋታቸው ለይተን እናያቸዋለን ።
2-  መጠኑ ይነስ እንጂ የማናዝንበት ሰው ላይኖር ይችላል ። ስለዚህ ሰዎችን አስቀድመን ይቅር ማለት አለብን ። አሁን ያሉትን ገፍተን ብንሄድ የሚቀጥለውም ጉድለት ያለበት ነው ። የይቅርታን ሕይወት መለማመድ ግን ከትግል ያድናል ።
 ጸሎት ለይቅርታ ወሳኝ ነው ። ይልቁንም የተቀየምናቸውን ሰዎች በጸሎት ላይ ስማቸውን እየጠራን ይቅር ብያለሁ ማለት ንጹሕ ልብን ያጎናጽፋል ። ከእመቤታችን ከድንግል ማርያም የምንማረው ይቅርታን ነው።
1-  አብረውን ኖረው ፥ አብረውን በልተው እንደ ጴጥሮስ የካዱን ቢኖሩ እኛም ይቅር ማለት አለብን ። ልዑል ራስ ካሣ ኃይሉ፡-
 “ወዳጅ ለክፉ ቀን ይሆናል አትበለው
 ስትያዝ ይከዳል ሰው የጴጥሮስ ልጅ ነው” ብለዋል ።
  2-  ሞታችንን አምነው መነሣታችንን የተጠራጠሩ ቢኖሩ እኛም ይቅር ማለት አለብን ። ተስፋ የቆረጡብን ፥ አበቃ ብለው የማጠቃለያ ዜና ያነበቡብን እጅግ ያሳዝኑናል ። ግን እግዚአብሔር ለክብሩ ካስነሣን ለበቀል የሚሆን ጊዜ ሊኖረን አይገባም ። አንድ ትልቅ አባት ፡- “እግዚአብሔር ከዚያ ኑሮ አንሥቶ ለዚህ ክብር ካበቃኝ ሌሎችን ለመቀየም እኔ ማን ነኝ? ብለዋል ።
 እመቤታችን ድንግል ማርያም ልጅዋ በመስቀል ላይ ይቅር ያላቸውን ከእርሱ ጋር በመተባበር ይቅርታ ሰጠቻቸው ። ይቅርታ የእግዚአብሔር ጠባይ ነው። እግዚአብሔር በእኛ ውስጥም ሊያገኘው ከሚፈልገው ነገር አንዱ ይቅርታ ነው ።
ቅዱስ አውግስጢኖስ ፡- “በእስጢፋኖስ ጸሎት ቤተ ክርስቲያን የጠፋውን ጳውሎስን አገኘች” ብሏል ። የእስጢፋኖስ ጸሎት የይቅርታ ጸሎት ነበር ። እስጢፋኖስ ሲወገር ልብሱን ይጠብቅ የነበረው የቀድሞው ሳውል የአሁኑ ጳውሎስ ነው /የሐዋ. 7፥54-60/ ። ጸሎቱ ሁለት ዓይነት ተጽእኖ አሳድሯል ። የመጀመሪያው ጳውሎስ በዚያ የፍቅር ኃይል እንዲነካ አድርጓል ። ሁለተኛ ጳውሎስ የሚመለስበትን ጸጋ አምጥቷል ። ጳውሎስ ኋላ ላይ የተመካው የእስጢፋኖስ ቤተሰብን በማጥመቁ ነው ። በልጃቸው ገዳይ እጅ የተጠመቁት የእስጢፋኖስ ቤተሰቦች የይቅርታ ሕይወት ነበራቸው ። “ከእስር ቤቶች ሁሉ ዘግናኙ እስር ቤት በተዘጋ ልብ ውስጥ መኖር ነው።”
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም