መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » የሰጠንን መስጠት

የትምህርቱ ርዕስ | የሰጠንን መስጠት

 

 

“ነገር ግን እንደ ክርስቶስ ስጦታ መጠን ለእያንዳንዳችን ጸጋ ተሰጠን ።” ኤፌ. 4 ፡ 7 ።

 

 

የሰጠንን መስጠት የያዝነው እንዲባረክ ያደርገዋል ። እሳት ራሱን አሙቆ አያውቅም ። ጸጋም ካልሰጠነው ይዳፈናል ፣ የማይጠቅምም ይሆናል ። እግዚአብሔር ያልሰጠን ነገር የለም ። በዓለም ላይ ትልቅ ክህደት ተቀብሎ አልተቀበልኩም ማለት ነው ። ተቀብሎ አልተቀበልኩም ማለት በቃል ብቻ ሳይሆን የሰጠንን ባለመስጠት የምንገልጠው ነው ። ተቀብለው አልተቀበልኩም የሚሉ የመጀመሪያው ባለማወቅ ያሉ ሲሆኑ ሁለተኛዎቹ እግሬ አቀረበልኝ ፣ እጄ ሳበልኝ የሚሉ ናቸው ። በእግዚአብሔር ሰጪነት ሳይሆን በልፋታቸው የሚመኩ ብዙዎች ናቸው ። እግዚአብሔር ሲሰጥ እንቀበለዋለን ፣ የእጃችንን ሥራ ሲባርክም እናከብረዋለን ። እግዚአብሔር አሥራት በኵራትን የሚጠይቀን ስለሰጠን ነው ። ካላስቀመጠበት የሚፈልግ አምላክ የለንም ። አሥራት ማውጣት ተቀብያለሁ ብሎ ማመስገን ነው ። አሥራት አለማውጣትም አልተቀበልኩም ብሎ መካድ ነው ። ትንሽ በነበራቸው ጊዜ አሥራት የሚያወጡ ብዙ ሲያገኙ ይሰስታሉ ። በብር አሥራት ያወጡ የነበሩ በዶላር ሲሆን ልባቸው ፈተና ውስጥ ይገባል ። የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር የቄሣርን ለቄሣር ማለት የእግዚአብሔርን አሥራት ፣ የመንግሥትን ግብር ስጡ ማለት ነው ። አሥራትና ግብር ትይዩ ሁነው ቆመዋል ። አሥራትም ግብርም ካለን ላይ የምንጠየቀው ነው ። አሥራትም ግብርም ብዙውን ለእኛ ይዘን ትንሹን የምንሰጥበት ነው ። አሥራት ለሰማይ መንግሥት ፣ ግብር ለምድር መንግሥት የምንሰጠው ነው ። ግብር አለማውጣት መንግሥትን አለመቀበል ነው ። አሥራት አለማውጣትም የእግዚአብሔርን መንግሥትነት መካድ ነው ። መንግሥት በግብር እንደሚተዳደር የእግዚአብሔር መንግሥትም በአሥራት ይተዳደራል ። ግብር አለማውጣት በአንዳንድ አገሮች አገርን ለማፍረስ የሚደረግ ወንጀል ተደርጎ በሞት ያስቀጣ ነበር ። አሥራት አለማውጣትም ቅጣት አለው ። የምንበላው ጣዕም ፣ የምንለብሰው ሙቀት ፣ የምንኖርበት ቤት መረጋጋት የሌለው ይሆናል ። አሥራትን የምንሰርቀው የምንኖረው በብዛት ስለሚመስለን ነው ። መኖር ግን በብዛት ሳይሆን በበረከት ነው ። አሥራትን የምናስቀረው አስልተን ለእኛ ሲያንስብን ነው ። ስሌት ሥጋዊነት ፣ አሥራት እምነት ነው ። ለእግዚአብሔር ያልሰጠነውን በእጥፍ ሌባ ይወስደዋል ፣ ላንድንበት በየሐኪም ቤቱ እንጨርሰዋለን ። ቀዳዳው ይባዛል ። እንዴት እንደመጣ እንጂ ገንዘቡ የት እንደሄደ አናውቅም ።

 

የሚገርመው አሥራት የብሉይ ኪዳን ትእዛዝ ነው ። ምድረ ከነዓንን ተቀብለው አሥራት በኵራት ማውጣት ካለባቸው በሰማያዊና በምድራዊ በረከት ተባርከን ከአሥራት የበለጠ ማውጣት አለብን ። አሥራት ስናወጣ ጥሩ ፈሪሳዊ እንሆናለን ፣ ከዚያ አለፍ ስናደርግ ደግሞ ክርስቲያን እንሆናለን ። በአውሮፓ በቀደሙት ዘመናት አሥራትን የሚሰበስበው መንግሥት ነበር ። ከእያንዳንዱ ሰው ደመወዝ አሥራትን ለቤተ ክርስቲያን ይቆርጥ ነበር ። ያ ልማድ ሆኖ አሥራት ማውጣት እስካሁን ድረስ የሕሊና ጥያቄ አይሆንባቸውም ። የግብጽ ክርስቲያኖችን ደመወዛቸውን ለቤተ ክርስቲያን ያሳውቃሉ ። ቤተ ክርስቲያንም ምን ያህል አሥራት እንደምታገኝ ታውቃለችና ታቅዳለች ። በሚቀጥለው ወር ላይ ተጨማሪ ገንዘብ የሚያገኝ ከሆነ ቤተ ክርስቲያኑ የበለጠ እንድታቅድ ያሳውቃል ። ታዲያ በየትም አገር ያለ የግብጽ ኦርቶዶክስ ክርስቲያን ሠላሳ ፐርሰንት ከቻለ ሰባ ፐርሰንት ቤተ ክርስቲያኒቱ ችላ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ይገዛሉ ። ለስደት ዘመን ብለው በአውሮፓና በአሜሪካ በአውስትራሊያ ለምእመናንዋ ብዙ ቤቶችን ትገዛለች ። አሥራት ስናወጣ ቤተ ክርስቲያንን የተከበረች እናደርጋታለን ። አገልግሎትን ከፍ አድርገነው ክርስትና እንዲስፋፋ እናደርጋለን ። ግብር የሚያወጣ የዚያ አገር ዜጋ ነኝ ማለቱ ነው ፣ አሥራት ማውጣትም የአማኝነትና የሰማይ ዜጋ ነኝ ማለት ነው ። የዲያብሎስን ያህል የእግዚአብሔር ሥራ እንዳይሠራ እንቅፋት የሚሆነው አሥራት የማያወጣ ምእመን ነው ። እንዴት ከዲያብሎስ ጋር ማመሳሰል ይቻላል ከተባለ ሁለቱም የእግዚአብሔርን ሥራ አስታጉለዋል ።

እግዚአብሔር የዘላለም ሕይወትን ብቻ ሳይሆን የዕለት ፍላጎታችንንም አሟልቶልናል ። መንግሥት ግብር ተቀብሎ አገርን ከወራሪና ከዘራፊ ይጠብቃል ፣ አሥራት በማውጣታችንም አገርንና ሕዝብን በጸሎት የሚጠብቁ አገልጋዮችን እንመግባለን ። ግብር ቅድመ ሁኔታ የሌለው ግዴታ ነው ። አሥራትም ቅድመ ሁኔታ የሌለው ግዴታ ነው ። የወር ወጪ የምናወጣው ለምንበላበት ቤት ነው ። እንዲሁም ቃሉን ለምንመገብበት አገልግሎት አሥራት ማውጣት ይገባል ። አሥራት ማውጣትን ለልጆቻችን ማስተማር አስፈላጊ ነው ። የነገው አገልግሎት በልጆቻችን የሚቀጥል ነው ። ልጆች ገና በጠዋቱ እግዚአብሔርንና አገልግሎትን ማፍቀር ይገባቸዋል ።

 

እግዚአብሔር ከድቃቂ ሣንቲም ጀምሮ ብዙ በረከትን ሰጥቶናልና በሰጠን ልክ መታመን ይገባል ። አሥራት በሕግ የተወሰነ ከአሥር አንድ ማለት ነው ። ከምናገኘው ሁሉ ከአሥር አንድ የእግዚአብሔር ነው ። በኵራት መጀመሪያ ላይ የምናገኘውን ልጅ ፣ ደመወዝና ከብት ሙሉ በሙሉ ለእግዚአብሔር መስጠት ነው ። መባ እንደ ፍላጎታችን ከአሥራታችን ውጭ የምንሰጠው ነው ። መባም ሦስት ክፍል አለው ። የመጀመሪያው ለእግዚአብሔር ሥራ ፣ ሁለተኛ ለአገልጋይ ፣ ሦስተኛ ለድሆች የሚሰጥ ነው ።

 

በሰጠን መጠን መታመን ይሁንልን !

 

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን

ነሐሴ 21 ቀን 2013 ዓ.ም.

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም