መግቢያ » መጽሐፍ ቅዱስ » አዲስ ኪዳን » ኤፌሶን ትርጓሜ » የተጠመቅን ሕዝቦች ነን

የትምህርቱ ርዕስ | የተጠመቅን ሕዝቦች ነን

“በበጎ ፈቃዱ እንደ ወደደ ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ለእርሱ ልጆች ልንሆን አስቀድሞ ወሰነን ።” ኤፌ. 1 ፡ 5 ።

እስካሁን ያለነው ቍጥር 5 ላይ ነው ። እግዚአብሔር እኛ ለመፍጠር ፣ እኛ ለማዳንና በልጅነት ጸጋ ለመቀበል ያስገደደው ነገር የለም ። የራሱ ፍቅር ግድ አለው እንጂ ። በራሱ ስለወደደን በእኛ አልጠላንም ። አስገድዶ ግን አያጸድቀንም ። በረከቱ ከእርሱ ሲሆን የመቀበያው እጅ ግን የእኛ ነው ። ቁም ነገራችን አስገደደው እንዳንል ገና ሳንፈጠር ወደደን ። ስለ ፍቅራችን ሞተ እንዳንል ጠላቶቹ ሳለን ነፍሱን ሰጠን ። እርሱ ንጉሥ ሳለ በባሪያ ወግ አልፈጠረንም ። መልኩን ፣ ጠባዩን የምንካፈል ፣ ርስቱን የምንወርስ ልጆቹ አድርጎ ፈጠረን እንጂ ። ወላጆቻችን እኛን እንደሚወልዱ አያውቁም ነበር ። የይሁዳ እናት ይሁዳን እንደምትወልድ ብታውቅ ኖሮ አትወልደውም ነበር ። እግዚአብሔር ግን ይሁዳን አውቆት እንዲወለድ አደረገው ። ወላጆች በቁማቸው ንብረታቸውን ለማውረስ ይቸገራሉ ። ሲሞቱ ግን ልጆች እንዲወርሱ ይናዘዛሉ ። እግዚአብሔር ግን ሞት የሌለበት ሳለ መንግሥቱን ያወረሰን ትልቅ አባታችን ነው ።

ዳግም ልደት ብለን ስንናገር ዳግም ያሰኘውን ሁለት ነገሮች ማንሣት እንችላለን ። ቀዳሚ በሌለበት ዳግም አይባልምና ። የመጀመሪያው አዳም ሲፈጠር የልጅነት ሀብት አግኝቶ ነበር ። ከሀብታት ሁሉ የልጅነት ሀብት ወይም ሀብተ ወልድና ስመ ክርስትና ይበልጣል ። ሌሎች ሀብታት ሁሉ የሚገኙት በዚህ ምክንያት ነውና ። የልጅነት ሀብት ከምድራውያን አማንያን ፣ ከሰማያውያን ቅዱሳን ጋር ቤተሰብ የሚያደርገን ነው ። እግዚአብሔር ሥራውን በእኛ የሚጀምረው በልጅነት ነው ። አዳም ግን ይህን ሲፈጠር በንፍሐተ መንፈስ ቅዱስ ያገኘውን ልጅነት በበደል ምክንያት አጎሳቆለው ። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ራሱን ቤዛ አድርጎ በመስጠቱ ይህ ልጅነት ተመለሰ ። የእግዚአብሔር መንፈስ ሳይሆን የእግዚአብሔር ልጅ ሥጋ መልበሱ ልጅነታችንን ለመመለስ ማሰቡን የሚያሳይ ነው ። በኢየሱስ ክርስቶስ ሥራ ልጆቹ የሆንበት ምሥጢር ዳግም ልደት ተብሎ ይጠራል ። በቀዳማዊ አዳም ቀዳማዊ ልጅነትን ስናጣ በዳግማዊ አዳም በክርስቶስ ዳግም ልደትን አገኘን ። እርሱ ከአብ ያለ እናት ከድንግል ያለ አባት በመወለዱ ሁለት ልደታትን ገንዘብ አድርጓል ። ሁለት ልደትን ገንዘብ ያደረገው ለዳግም ልደት አበቃን ።

ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔር መንግሥት አማናዊት ጥላ ወደምትሆን ቤተ ክርስቲያን የምንገባው በዳግም ልደት ወይም በመጠመቅ ነው ። ዳግም ልደት የሚያሰኘው ሁለተኛው አመክንዮ ከእናት ከአባታችን ተወልደን ይህን ዓለም ያየንበት ጸጋ እንደ ቀዳማዊ ልደት ይቆጠርና ከውኃውና ከመንፈሱ የተወለድንበት መንፈሳዊ ልደት ደግሞ ዳግም ልደት ይሰኛል ። ለመወለድ ሁለት ነገሮች መተባበራቸው ግድ ነው ። እንዲሁም በመንፈሳዊ ዓለም ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ፣ ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ እንወለዳለን ። በሥጋ ተወልደን ይህን ዓለም እንዳየን ፣ በመንፈስ ተወልደን መንፈሳዊውን ዓለም እናያለን ። /የበለጠ ለመረዳት “ኒቆዲሞስ” የተሰኘውን የዲያቆን አሸናፊ መኰንን መጽሐፍ ያንብቡ ።/

የእግዚአብሔር አሳቡ ከልካይ ፣ ተጋፊ ፣ ሻሪ የለውም ። ስለዚህ አስቀድሞ ለልጅነት አስቦን ሳለ ከባሪያ እንኳ አንሰን ተገኘን ። ስለ ተፈጠርን እንኳ መገዛት ሲገባን ስለ ተወደድንና ልጆች ስለሆንም መታዘዝ አቃተን ። በዚህ ምክንያት በዳግም ልደት ልጆቹ የምንሆንበትን መንገድ አዘጋጀ ። እግዚአብሔር እኛን ለማዳን አስቦ አልቀረም ። በመስቀል ላይ በመሞት ፍቅሩን ገለጠልን ። አሳብ ወደ ተግባር ካልተለወጠ ሰውን ማዳን እንደማይቻል አስተማረን ። ወደ ተግባር ሲለወጥ ደግሞ ዝቅ ማለት ፣ መሰቀልና መሞት ያስፈልጋል ። ብዙ አሳብ አለኝ እያሉ ስለ ራእያቸው የሚናገሩ ሰዎች አሉ ። የማይታየው አምላክ የሚታይ ሥጋ የለበሰው ረቂቁ አሳብ መግዘፍ ስላለበት ነው ። የአሳብ ቸርነት ለችግረኛ ጥርኝ ውኃ አይወጣውም ። የአሳብ ፍልሚያ ምርኮኛውንና የኃጢአት ባሪያ የሆነውን የሰው ልጅ ነጻ አያወጣውም ። ከሺህ አሳብ አንድ ተግባር ሕይወት ትለውጣለች ። ጉዞ እስካልተጀመረ ሁሉም ነገር ሩቅ ነው ። ያየነው የሚታየን መንገድ ስንጀምር ነው ። እግዚአብሔር ሰውን ከአፈር ፈጥሮ ልጁ አደረገው ። ሰው ለራሱ ሰው ፣ ለእግዚአብሔር ልጅ ሆነ ። ጭቃን ልጄ ያለ አምላክ ቡሩክ ነው ። ጭቃ የሆነውን ኃጢአት የሚያላቁጡትን አንሥተን ልጄ ማለት ዛሬ የቀረልን ጸጋ ነው ። የሰው ሕይወት ሲለወጥ ከማየት የበለጠ ደስታ የለም ።

ከቤተሰቦቻችን ስንወለድ አናውቃቸውም ፣ አናምናቸውም ፣ አንወዳቸውም ነበር ። ሁሉም ነገር ከእነርሱ ሆኖ ቆይቶ አወቅናቸው ፣ አመናቸው ፣ ወደድናቸው ። እንዲሁም በልጅነታችን ብንጠመቅም ኑሮአችን በቤቱ ነውና እግዚአብሔርን እያወቅነው ፣ እያመነው ፣ እየወደድነው እንመጣለን ። ሰይጣን እንኳ በማለዳ መግባት አስፈላጊ መሆኑን አውቆት ከመጠመቁ በፊት ለእኔ ልጃችሁን ስጡኝ የሚላቸው ወገኖች አሉ ። ልጆቻቸውን ወደ ጥምቀት ያላቀረቡ ፣ በጠዋት እንዲገቡ ያላደረጉ እስከ ማታ ሊያጡአቸው ይችላሉ ። ደግሞ ክርስቶስ የሞተውና የተነሣው ለሕፃናትም ነው ። የክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ መመስከሪያ የሆነው ጥምቀትም ለሕፃናት ይገባል ።

የኤፌሶን መልእክት ትርጓሜ /11

ዲያቆን አሸናፊ መኰንን
የካቲት 17 ቀን 2014 ዓ.ም.

እባካችሁ ለሌሎች አካፍሉት

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም