መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » ምክር ለሰሚው » ምክር ለሰሚው/14

የትምህርቱ ርዕስ | ምክር ለሰሚው/14

ወዳጄ ሆይ !

ሥራ ከደመወዝ ባሻገር ደመወዝ አለው ። በማለዳ የሚያነቃህ ፣ ንጹሕና ውብ እንድትሆን የሚያተጋህ ፣ የክት ልብስህን የሚያስለብስህ ፣ ቁርስህን በሰዓቱ የሚያስቀምስህ ፣ ከቤትህ እንድትወጣ የሚያደርግህ ፣ ከሰዎች ጋር የሚቀላቅልህ ፣ ማኅበራዊ ኑሮ የሚሰጥህ ፣ የገሀዱን ዓለም እውነት የሚያሳውቅህ ፣ ብዙዎችን እንድትረዳና እንድታስደስት ዕድል የሚሰጥህ ፣ ታዛዥነትን የሚያስተምርህ ፣ እውቀት የሚጨምርልህ ፣ በተስፋ የሚያኖርህ ፣ ስለ ጡረታ የሚያሳስብህ ፣ ደመወዝ አለኝ ብለህ እንድትበደር የሚያደርግህ ፣ ሰዎችም አምነውህ የሚያበድሩህ ፣ ይሠራል ተብለህ የሚያስከብርህ ፤ አእምሮህን በእውቀት ፣ ጉልበትን በኃይል የሚሞላልህ ፣ የጤንነትህና የጉብዝናህ ምስክር ፣ ለማግባት ሽማግሌ ስትልክ “ምንድነው ሥራው?” ስትባል ዋስ የሚሆንልህ ፣ ሥራህ ነው ።

ሌተቀን በቤትህ ብትኖር ትሰለቻለህ ፣ ከትዳር ጓድህ ጋር ታጋጫለህ ፣ የልጆችህን ልግመኛነት መቀበል ይከብድሃል ። ሰውነትህ እንቅስቃሴ ስለማያደርግ ይተሳሰራል ፣ ለበሽታ ትጋለጣለህ ። ሥራህ ያልተነገረለት ደመወዝ አለው ። ሥራህን በማይለካ ጸጋው እንጂ በሚቆጠረው ብር አትለካው ። እሰይ ሰኞ መጣ በል ። ቤተሰብህም የሚያከብርህ ስትሠራ ነውና ። እግዚአብሔርም የሚባርከው የእጅህን ሥራ ነው ። ሥራ የኋላ እርግማን ሳይሆን የተፈጠርህበት ምክንያት ነው ። ሥራን ስትጠላ መብልን አብረህ ጥላ ።

አባቶች ሁሉ እንደ ተናገሩት ክፉ አሳብ በሥራና በጸሎት ይርቃል ። ሥራ ብታጣ እግዚአብሔር የገዛ አካልህን ሥራ አድርጎ ሰጥቶሃል ። “እኔ ለእኔ ሥራ ነኝ” በል ። ፀጉር ማበጠር ፣ ፊትን መታጠብ ፣ ጥርስን መፋቅ .. የገዛ ገላህ ሥራ ሁኖ ተሰጥቶሃል ። ሥራ ብታጣ ንጹሕ ልብስህን እንደገና እጠበው ። አካባቢህን ተንከባከብ ፣ አበቦችን ውኃ አጠጣ ። ሥራ ጭንቀትን ያቀላል ፣ የአእምሮ መወጠርን ያፍታታል ። አዲስነትን ያጎናጽፋል ። የምታዝዛቸው ሠራተኞች ሲበረቱ ያንተ ጉልበት ግን መላሸቁን ተመልክተህ ሥራ መሥራትን ውደድ ። ሠራተኞችህ ጤነኞች አንተ ግን በብዙ የኪኒን ጉቦ እንደምትኖር እያሰብህ አኗኗርህን አስተካክል ። ጌትነት መሥራት እንጂ በቁም መሞትና የሰው ሸክም መሆን አይደለም ። እግዚአብሔርን ለምነህ ያገኘኸውን ሥራ ሰውን ማስለቀሻ አታድርግ ፣ ቅጣቱን አትችለውም ። ዘመናዊነት ጌትነት ሳይሆን አገልጋይነት ነው ። ነገሥታት መንገድ ሲያጸዱ በሚታይበት ዘመን ሥራ ክቡር መሆኑን ተረዳ ። ሳትሠራ የሚከፍሉህ ሞትህን እያፋጠኑ ነውና በግድ መሥራትን ጠይቅ ። ሥራ አለኝ ብሎ ከቤት መውጣት ጸጋ መሆኑን ተረዳ ።

ወዳጄ ሆይ !

የምሠራው የማይሠሩ ወንድሜንና እኅቴን ለመርዳት ፣ ለእነርሱ የተሻለ አገር ለመፍጠር ነው ብለህ አስብ ። ጎበዝ ሁኖ ሥራ ያጣ ፣ ሰነፍ ሁኖ በሥራ የሚቀልድ ፣ ወሬ እያቀባበለ ፣ የአለቃውን ያልቆሸሸ ቀሚስ እያራገፈ የሚኖር አድር ባይ አለ ። አገራችን የሚሠራውን ንቃ ፣ የሚያወራውን የምታከብር ፣ የሙያ ሳትሆን የቡድን አገር ከሆነች ሰንብታለች ። ባዶ ወረቀትና አድር ባይ አንድ ነው ። ሁለቱም መልእክት የለሽ ናቸው ። ሐውልት እንኳ ይናገራል ። አድር ባይ ግን ባዶ ነው ። ከሥራህ ላይ ቤተ ክርስቲያን ሳትጠይቅህ አሥራት አውጣ ፣ ጉዳተኛው ወገንህ ሳይለምንህ መባውን ስጠው ። ይህ ውለታ ሳይሆን አንተ ጋ የተቀመጠ መብቱ ነው ። የውሸት ምክንያት ፈጥሮ የሚለምንህን እዘንለት ። እንዲዋሽ ያደረገው ያንተ ጨካኝነት ነው ።

ወዳጄ ሆይ !

ከመምራት መመራት ፣ ከማዘዝ መታዘዝ ይሻላል ። መሪ ያልሠራውን መልካም ነገር የራሱ አድርጎ በሌላው ጉልበት ይዘመርለታል ፣ ባልሠራውም ክፉ ሥራ ሲወቀስ ይኖራል ። ሙሴ የራሱን መቃብር እንደ ቆፈረ መሪ ስትሆን ጉድጓድ ቆፍሮ የሚቀብርህ የለምና መቃብርህን እየቆፈርህ እንደሆነ አስተውል ፤ ስትጨርስ ትወድቃለህ ። ማዘዝም በልግመኛ ትውልድ መካከል በሽተኛ ያደርጋልና አትምረጠው ። ስለ ነገሩ እውቀት በሌለህ ነገር ተቋም አትክፈት ። አለማወቅህን ካወቀ ሠራተኛም ይንቅሃል ።

ወዳጄ ሆይ !

ከአፈርነት የተነሣህ ሰው ፣ ወደ አፈር የምትመለስ ትቢያ መሆንህን አስበህ ለቆመው ክብር ፣ ለሚሞተው የሰውነት ሽኝት አትንሣ ። ማድረግ ባትችል በአሳብ እርዳ ። መርዳት እየቻልህ አሳብ አታብዛ ። አንተም ሞት አለብህና በሞተው ደስ አይበልህ ። የሚያረፍድ እንጂ በዓለም የሚቀር ሰው የለም ። ልጆችህ የአባቴ ልጅ ፣ የእናቴ ልጅ እያሉ እንዳይከፋፈሉ ሥራ ቀናልኝ ብለህ ሁለት ትዳር አትያዝ ። ደስታህን ብቻ ሳይሆን የሌሎችንም መሻት አዳምጥ ። ላትፈጽም እሺ ብለህ ሰውን አታደንዝዝ ፣ በጊዜው የሆነ እንቢታ የውለታ ያህል ነው ።

መጻፍ የማይቻልበት ዘመን አለና እጽፋለሁ ፣ ማንበብ የማይቻልበት ዘመን አለና አንብቡ !!!

በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም