መግቢያ » ልዩ ልዩ አንድ » እንዲህ ቢሆንስ » እንዲህ ቢሆንስ …? /9/

የትምህርቱ ርዕስ | እንዲህ ቢሆንስ …? /9/

“በአእምሮዬ ውልብ የሚሉ የኃጢአት አሳቦች አሉ ። አሳቦቹ ምኞት ቀጥሎ ፈቃድ እንዳይሆኑ እሰጋለሁ ። ይህ ስሜት ውስጤ ላይ ሲነሣ በክርስትና የምዘልቅ አይመስለኝም ። ወደ ቀድሞ ሕይወቴ ብመለስስ እያልሁ እፈራለሁ” እያልህ ይሆን ? የክርስትናን ጉዞ የጀመርከው በልጅነት ጸጋ ነው።እግዚአብሔር ከሰጣቸው ጸጋዎች የበላይ የሆነው የልጅነት ጸጋ ነው ። ያንተ ልጅነት እንደ ክርስቶስ ያለ ልጅነት አይደለም ፣ የእርሱ ልጅነት አብን በመልክ የሚመስልበት ፣ በባሕርይ የሚተካከልበት ነው ። ያንተ ልጅነት የጸጋ ሲሆን የተወለድኸውም ከሥላሴ ነው ። ይህ ልጅነትህ እግዚአብሔርን በመምሰል የተፈጠርህበት መዐርግ ነው ። ይህ ልጅነትህ በክርስቶስ እንደገና የተመለሰልህ ርስትህ ነው ። ሳይንስና እምነት ፍጹም የተለያዩ ናቸው ።ሳይንስ በውርደት ይጀምራል ፣ አንተ እንስሳ ነበርህ ይላል ፤ እምነት ግን አንተ በእግዚአብሔር መልክ ተፈጥረሃል በማለት በክብር ይጀምራል ። ሳይንስ የሚቀጥለውም በውርደት ነው ፣ እምነት ግን መንግሥቱን ትወርሳለህ ይላል ። ከእግዚአብሔር መወለድ ትልቅ ክብረት ነው ። ልጅ በታላቅ ፍቅር ይወደዳል ፣ አንተም በአጋፔ ፍቅር ተወደሃል ። ልጅ ይወርሳል ፣ አንተም ወራሽ እንድትሆን ተጠርተሃል ። ልጅ ቢያጠፋ ልጅነቱ አይፈርስም ፣ ኅብረቱ ግን በይቅርታ ይታደሳል ። አንተም ብታጠፋ ንስሐ የተባለ የሕይወት ሳሙና ተዘጋጅቶልሃል ። ልጅ የሚወደደው ፍጹም ስለሆነ አይደለም ፣ ወደ ፊትም ጥሩ ይሆናል ተብሎ አይደለም ። ልጅ ስለሆነ ነው ። አንተም የምትወደደው ልጅ ስለሆንህ ነው ።
አእምሮ ማለት እንደ አደባባይ ነው ። በአደባባይ ዛሬ የሚያልፉት እነማን እንደሆኑ በርግጠኝነት መናገር አይቻልም ። በአእምሮም የሚታሰበው እንዲሁ ነው ። በደጃችን የሚያልፉትን ሁሉ ጎራ በሉ አንልም ፣ በኅሊናችን የሚያልፈውን ሁሉም ማስተናገድ የለብንም ። በደጃፋችን ላይ ክፉ ሰዎች ሊያልፉ ይችላሉ ፣ በኅሊናችንም ክፉ አሳቦች ሊያልፉ ይችላሉ ። በደጃፋችን ላይ የሚያልፉ ክፉ መሆናቸውን ስናውቅ በራችንን እንዘጋለን ፣ በኅሊናችንም ክፉ አሳብ ሲመጣ በጸሎት ልባችንን መጠበቅ ይገባናል ። “ወፎች በጭንቅላታችን ላይ እንዳይበሩ መከልከል አንችልም ፣ አናታችን ላይ ግን ጎጆአቸውን እንሥራ ቢሉ አንፈቅድላቸውም ።”
ሰይጣን ክፉ አሳቦችን እያመጣ የሚሟገተን የመጀመሪያው አሳቡን ተቀብለን ወደ ምኞትና ፈቃድ እንድንወስደው ነው ። ሁለተኛው “እንዴት እኔ ይህን አስባለሁ ?” በማለት እንድንሸማቀቅ ነው ። በዚህ ክፉ አሳብ ሁነህ እንዴት ትጸልያለህ ፣ እንዴት ከክርስቲያኖች ጋር ትገናኛለህ ይለናል ። ነገር ግን ባንጸልይም ያለነው በእግዚአብሔር መዳፍ ላይ ነው ። ዓለምን በመሐል እጁ የያዘው ጌታ ነው ብለን ካመንን እኛም ያለነው በመዳፉ ላይ ነው ። ክርስትና ሁለት ነገሮችን ሁልጊዜ ይጠይቀናል ። የመጀመሪያው የምናኔ ሕይወትን ነው። ይህም ዓለምን መናቅና በነጻ ሰዎችን ማፍቀር ነው ። ሁለተኛው ተጋድሎ ነው ። ከክፉ አሳብ ፣ ከክፉ ሰዎችና ከክፉ ዘመን ጋር እንታገላለን ።በአእምሮአችን የሚመጡትን ክፉ አሳቦች የጦር ዕቃችን በሆነው በእግዚአብሔር ቃል ፣ በጸሎት ፣ በጌታችን ስምና ሥልጣን ልንታገል ይገባል። መጽሐፍ ተጋደሉ ይላል ። ከክፋት ጋር ካልተጋደልን ከሰዎች ጋር እንጋደላለን ፣ ከክፉ ምኞት ጋር ካልተጋደልን ከፍቅር ጋር እንታገላለን ።
በአእምሮአችን የሚያልፉት አሳቦች ሁሉ የእኛ ላይሆኑ ይችላሉ ። ስለዚህ ነቅተን በእግዚአብሔር ስም መገሠጽ ይገባናል ። አእምሮአችን ላይ ያለውን አሳብ በእርሻ ላይ እንዳለ እህል መቊጠር ይቻላል ። በእርሻ ላይ ያለ እህል አረም ፣ ገለባ ፣ እንክርዳድ አለው ። አረሙ እህሉ ሳይታጨድ ፣ ገለባው እህሉ ሲወቃ ፣ እንክርዳዱ እህሉ ሲለቀም የሚወገድ ነው ። ሁሉም ጠላት በአንድ ጊዜ አልተወገደም ። እንደ አረሙ የሚመጡ ልዩ ልዩ አሳቦች በእግዚአብሔር ስም ማራቅ ይገባል ። እንደ ገለባው አንዳንድ አሳቦች በምክር የሚወገዱ ናቸው ። እንደ እንክርዳዱ በልዩ እውቀትና በጸሎት የሚወገዱ አሳቦች አሉ ። ውልብ የሚሉብን አሳቦች ከዚህ በፊት አስበናቸው የማናውቃቸው ሲሆኑ እነርሱን ላለማሰብ የምናደርገው ጥረት የበለጠ እንድናስባቸው ሊያደርገን ይችላል ። በእግዚአብሔር ስም በመገሠጽ ሌላ አሳብ ማሰብ ይገባናል ። አንድን ክፉ አሳብ ላለማሰብ መጣር የበለጠ ወደ ማሰብ ያደርሳል ። አሳብ ግን በአሳብ ይሻራል ። እንደ ገለባው ያሉ አሳቦች ደግሞ በልዩ ረገጣ የሚረግፉ ፣ በመንሽ የሚበተኑ ናቸው ። አንዳንድ አሳቦች በመከራና በፈተና የሚወገዱ ናቸው ። መከራ የኃጢአትን እሾህ ያቃጥላል ።መከራና ፈተና የሚያስወግዱት ክፉ አሳብ አለ ። እንክርዳዱ ግን ሁለቱንም ደረጃዎች ያለፈ ሲሆን በባለሙያ በንቁ ዓይን የሚወገድ ነው ። ይህም በጾምና በጸሎት በረድኤተ መንፈስ ቅዱስ የሚወገድ ነው ።
ከአሳብ ሲያልፍ ስሜታችንን የሚነካ ነገር ሊገጥም ይችላል ። ይህ ስሜት እንዴት ተሰማኝ ? ይህ ከተሰማኝ እኔ የተፈጠርኩት ለዚህ ነው በሚል አሳብ ስሜትን እንደ ቃለ እግዚአብሔር ማመን ተገቢ አይደለም ። የተሰማን ሁሉ ትክክል አይደለም ። ያልተሰማን ሁሉም ክፉ አይደለም ። ስሜትን ማመን ከባድ ነው ። ስሜት አሁን ተጋግሎ ኋላ የሚበርድ ለጸጸት አሳልፎ የሚሰጥ ነው ። ስሜት መጀመሪያ እንጂ መጨረሻ የለውም ።
ሕይወት የትግል እንጂ የመዝናኛ ሜዳ አይደለችም ። ትግል ሲመጣ ከፈራህ የበለጠ እጅ እየሰጠህ ትመጣለህ ። በድፍረት በገደል አፋፍ ላይ የሚሮጡ አሉ ፣ በፍርሃት በሜዳ ላይ የሚወድቁ አሉ ። በገመድ ላይ የሚጓዙ ደፋሮች ባሉበት ዓለም ከወንበር ላይ የሚወድቁ ፈሪዎች አሉ ። ፍርሃት ለጠላት ምልክት የሚሰጥ ነው ። ፍርሃት የሰይጣን መግቢያ በር ነው ።
ክርስትናን የሚያስጀምር እግዚአብሔር እንደሆነ የሚያስፈጽምም እርሱ ነው። ከጠላት ብቻ ሳይሆን ከራስህም ያድንሃል ። የእግዚአብሔር ፍቅር አቅም ሁኖ የፈራኸውን ትረግጣለህ ፣ ያሸነፈህን ድል ትነሣለህና በርታ ።
ወደ ክርስቶስ መገስገስ 14
ተጻፈ አዲስ አበባ
ጥቅምት 20 ቀን 2011 ዓ.ም.
በማኅበራዊ ሚዲያ ያጋሩ
ፌስቡክ
ቴሌግራም
ኢሜል
ዋትሳፕ

ተዛማጅ ትምህርቶች

የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ
የትምህርቱ ርዕስ

መጻሕፍት

በዲያቆን አሸናፊ መኰንን

በTelegram

ስብከቶችን ይከታተሉ

አዳዲስ መጻሕፍት

ትርጉሙ:- ቀይ ዕንቈ

ለምድራችንና ለአገልግሎታችን በረከት የሆነ መጽሐፍ
የመጀመሪያ እትም ጥቅምት 2016 ዓ.ም

1ኛ ጢሞቴዎስ ትርጓሜ – ክፍል አንድ

የመጀመሪያ እትም ሐምሌ 2013 ዓ.ም

ምክር አዘል መጽሐፍ

የመጀመሪያ እትም